የግብርናውን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የግብርና ባለሙያዎች ሚና የጎላ መሆኑን የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ አስታወቀ

የግብርና ምሰሶዎችን በማሳካት የበለጸገ ቤተሰብ ለማየት እተጋለሁ በሚል መሪ ቃል የማእከላዊ እትዮጵያ ክልል ግብርና ትራንስፎርሜሽን አቅጣጫዎች ለግብርና ልማት ሠራተኞች ስልጠና በወራቤ እየተሰጠ ይገኛል።

የሀገሪቱን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በዘርፉ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውንና በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የተለያዩ ኢኒሼቲቮች ተቀርጸው ውጤት ማምጣት እየተቻለ መሆኑን በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማእረግ የግብርናና ገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪ እና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡስማን ሱሩር ተናግረዋል።

በዘርፉ እየተመዘገቡ ለሚገኙ ውጤቶች ባለቤት በዋናነት የግብርና ባለሙያዎች መሆናቸውን ነው አቶ ኡስማን ሱሩር እውቅና የሰጡት።

የግብርናውን ምርትና ምርታማነት በማሳደግ ድህነት ውስጥ የሚገኘውን ማህበረሰብ ወደተሻለ የኑሮ ደረጃ ማሸጋገር እንደሚቻል አቶ ኡስማን ሱሩር ገልጸዋል።

የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ምርትና ምርታማነት በስልጤ ዞን ማሳደግ መቻሉን ነው የስልጤ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊና ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ሙበረ ከማል የተናገሩት።

በዞኑ በቡናና ቅመማ ቅመም ምርቶችን ከአካባቢው ፍላጎት አልፎ ለውጭ ሀገር ኤክስፖርት በማድረግ ለሀገሪቱ የውጭ ምንዛሪ ማስገኘት መቻሉንም አቶ ሙበረ ገልጸዋል።

በዘርፉ ሰፋ ያሉ ውጤቶችን ለማስመዝገብ በቀጣይ ምርት ዘመን የግብርና ማነቆ የሆኑ ችግሮችን በመለየት ወደ ተግባር እንደሚገባም ተናግረዋል፡፡

በክልሉ ከ7 ሺህ 200 በላይ የግብርና በለሙያዎቹ ስልጠና እንደሚወሰዱ ተገልጿል፡፡

ዘጋቢ፡ አብድልሀፊዝ መሐመድ