ብቁና ስልጡን ሲቪል ሰርቫንት ለማፍራት የተሻሉትን ማበረታታት እንደሚገባ ተገለፀ
ሀዋሳ፡ ሰኔ 19/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በጌዴኦ ዞይ የይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር ሲቪል ሰርቫንትና ሰው ሀብት ልማት ጽ/ቤት በተሻለ አፈፃፀም ፊት ለወጡ ተቋማትና ግለሰቦች የዕውቅናና ሽልማት መርሃ-ግብር አካሂዷል።
በመርሀ ግብሩን ላይ መልዕክት ያስተላለፉት የይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ታደለ ጥላሁን፥ በቡና ምርቷ ዓለም አቀፍ እውቅና ያላት የይርጋጨፌ ከተማ የማደግ ሰፊ ዕድል ቢኖራትም ያሉ ዕድሎችን አዋህዶ ካለመጠቀም የተነሳ ዕድገቷ ሲጓተት መቆየቱን አስታውቀዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት ያሉ ምቹ ዕድሎችን ወደ ድል ለመቀየር የሚያስችሉ ሀብት፣ ዕውቀትና ዘመኑን የዋጁ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የከተማዋን ዕድገት ለማፋጠን ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
እስከ አሁን ላስመዘገብናቸው ተስፋ ሰጪ ውጤቶች የከተማው ሲቪል ሰርቫንት ሚና ከፍተኛ እንደነበር ያስታወሱት አቶ ታደለ፥ ሁሉንም መሸለም ባይቻል እንኳን በይበልጥ ወደ ፊት የወጡትን ለይቶ ዕውቅና መስጠት ለቀጣይ ተግባር የሞራል ስንቅ እንደሚሆን አብራርተዋል፡፡
የከተማው ሲቪል ሰርቪስና ሰው ሀብት ልማት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ዳዊት የጋ በበኩላቸው የሠራተኞችን የትምህርት መረጃ ከማጥራት አንስቶ በባህሪና ተግባር መዝኖ ተገቢውን ውጤት በመስጠት የፓብሊክ ሰርቫንቱን የመፈፀም አቅም ለማጎልበት በትኩረት እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
እስከ አሁን በተሠራው የላቀ አፈፃፀም ላስመዘገቡት ዕውቅና የመስጠቱ ፣ የተያዙትን ዕቅዶች ለመፈፀም እየተጉ ያሉትን ማበረታታትና በዲጂታል የታገዙ አሠራሮችን በመዘርጋት ከተማዋን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ዕውቅናና ሽልማት የተበረከተላቸው አካላትም ባገኙት ክብር ሳይኩራሩ ለተሻለ ነገ እንደሚተጉ ተናግረዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ሳሙኤል በቀለ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን
ብቁና ስልጡን ሲቪል ሰርቫንት ለማፍራት የተሻሉትን ማበረታታት እንደሚገባ ተገለፀ

More Stories
ባለፉት 11 ወራት ብቻ በቤንች ሸኮ ዞን በትራፊክ አደጋ የ32 ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተገለጸ
የሆቴሎችን ደረጃ የሚያስጠብቅ ስራ በመስራት ላይ እንደሚገኝ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ባህል ቱሪዝም ቢሮ ገለፀ
ሁሉም የሕብረተሰብ ክፍል አረጋውያንን በመደገፍ ለራሱ ስንቅ ሊያስቀምጥ እንደሚገባ የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ዳዊት ሀዬሶ ገለጹ