ሁሉም የሕብረተሰብ ክፍል አረጋውያንን በመደገፍ ለራሱ ስንቅ ሊያስቀምጥ እንደሚገባ የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ዳዊት ሀዬሶ ገለጹ

ዩኒቨርሲቲው ለሜሪ ጆይ ሆሳዕና የአረጋውያን ማዕከል የአልጋ ድጋፍና የአረንጓዴ አሻራ የማኖር ተግባር አከናውኗል።

የሜሪጆ ኢትዮጵያ የሆሳዕና አረጋውያን ማዕከል በበኩሉ የዋቸሞ ዩኒቨርስቲ እያደረገ ያለው ዘርፈ-ብዙ ድጋፍ ለሌሎች ተቋማትና ግለሰቦች ምሳሌ ሊሆን የሚችል እንደሆነ ጠቁመዋል።

የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ በሜሪ ጆይ ኢትዮጵያ የሆሳዕና አረጋዊያን ማዕከል ያከናወነውን የችግኝ ተከለ መርሃ-ግብር ያስጀመሩት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ዳዊት ሀዬሶ፤ ተቋሙ በሆሳዕና ከተማ እየተገነባ ያለው የአረጋውያን እና ሕጻናት ማዕከል ደረጃ በጠበቀ መልኩ በፍጥነት ተገንብቶ ለአገልግሎት እንዲውል ለማስቻል ግንባታ ከጀመረበት ዕለት ጀምሮ በገንዘብ፣ በቁሳቁስ እና በሙያ እየደገፈ መሆኑን ተናግረዋል።

ተግባሩ የመንፈስ እና የሞራል ዕርካታ የሚሰጥ ስለሆነ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ያረጋገጡት ፕሬዚዳንቱ፤ ሁሉም የሕብረተሰብ ክፍል አረጋውያንን በመደገፍ ለራሱ ስንቅ ሊያስቀምጥ ይገባል ብለዋል።

የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የአስተዳደርና ልማት ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ኤርሚያስ ሞሊቶ በበኩላቸው፤ በወጣትነት ዕድሜያቸው ሕዝብንና አገርን እያገለገሉ ቆይተው ጧሪና ቀባሪ በማጣት የሚንገላቱትን ለመሰብሰብ እየተደረጉ ያሉት ዘርፈ-ብዙ ተግባራት ግብ እንዲመቱ ዩኒቨርሲቲው የአንበሳውን ሚና እየተጫወተ እንደሆነ አንስተዋል።

በዕለቱ የተተከሉ የጥላ እና የፍራፍሬ ዛፎች አረጋውያኑ ከጥላነት ባለፈ ለምግብነትም እንዲጠቀሙ ታሳቢ ያደረገ እንደሆነ ያወሱት ዶ/ር ኤርምያስ፤ የአልጋ፣ የጥራጥሬ እህሎች እና ሌሎችም ቁሳቁሶች ለማዕከሉ ድጋፍ መደረጋቸውን አመልክተዋል።

በሜሪ ጆይ ኢትዮጵያ የሆሳዕና ማዕከል ተወካይ ወ/ሮ አሰለፈች አሰፋ፤ የተቋሙ ግንባታ ከመሠረት ጀምሮ አሁን ያለበትን ደረጃ እስኪደረስ የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ አስተዋጽኦ የጎላ መሆኑን ጠቅሰው ሌሎች ተቋማትም የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ አርአያነት እንዲከተሉ ጠይቀዋል።

ዘጋቢ: ጌታቸው መጮሮ – ከሆሳዕና ጣቢያችን