ሴቶች በሁሉም ዘርፍ የነቃ ተሳትፎ ማድረግ እንዳለባቸው የይርጋጨፌ ወረዳ አስተዳደር አስገነዘበ

በወረዳው በተሠሩ ሥራዎችና በቀጣይ ተግባራት ላይ የሴቶች ሚናን ትኩረት ያደረገ ውይይት ከወረዳው ሴክተር መስሪያ ቤቶች ሴት የመንግስት ሰራተኞች ጋር ውይይት ተደርጓል።

የይርጋጨፌ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ቡኔ በመድረኩ እንደተናገሩት፤ ሴቶች እንደ ሀገር በሚሠሩ ሥራዎች በሁሉም ዘርፍ የነቃ ተሳትፎ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል።

በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ዘርፍ ምቹ ሁኔታዎች አሉ የሚሉት አስተዳዳሪው፤ ይህን ምቹ ነባራዊ ሁኔታ መጠቀም አለባቸው ብለዋል።

ሴቶችን ለመደገፍ ምቹ ሁኔታዎች እየተፈጠሩ መሆናቸውን ያመላከቱት አቶ ዳዊት ቡኔ፣ ዘመኑ የውድድር በመሆኑ በሁሉም ዘርፎች ተወዳዳሪ መሆን እንደሚያስፈልጋቸው አሳስበዋል።

ሴቶች በየተቋማቸው ያለውን መልካም ጅማሮዎችን ማስቀጠልና ደካማ ጎኖችን ለማረም መሥራት እንዳለባቸው ተናግረዋል።

የወረዳው ሴቶችና ህጻናት ጉዳዮች ጽ/ቤት ኃላፊ ወ/ሮ የምስራች ከፍያለው፤ መድረኩ ከወረዳው አስተዳደር ጋር በመተባበር የተዘጋጀ መሆኑን ገልጸው በቀጣይ በሚሠሩ የልማት ሥራዎች የሴቶችን ሚና የሚያጠናክር መሆኑን ገልጸዋል።

ወ/ሮ መስተዋት ጥላሁን፣ ዘማነሽ ኤዴማ እና ሌሎችም በሰጡት አስተያየት፤ በወረዳው እየተሠሩ ያሉ የልማት ሥራዎች መጠናከር እንዳለባቸውና በተለያዩ ዘርፎች ጠንካራ ሴቶች በመኖራቸው ተሳትፏቸውን ማሳደግ እንደሚያስፈልግ አመላክተዋል።

ዘጋቢ: እስራኤል ቅጣው – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን