የሀዲያ ዞን ምክር ቤት 2.8 ቢሊየን ብር ተጨማሪ በጀት አጸደቀ

የሀዲያ ዞን ምክር ቤት 2.8 ቢሊየን ብር ተጨማሪ በጀት አጸደቀ

ሀዋሳ፡ ሰኔ 26/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሀዲያ ዞን ምክር ቤት ባካሄደው 4ኛ ዙር 13ኛ ዓመት 7ኛ አስቸኳይ ጉባኤ የ2018 ተጨማሪ በጀት ከ2 ቢሊዮን 8 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት አጽድቋል።

በመንግሥት የሚመደቡ በጀቶች ለታለመላቸው ዓላማ እንዲውሉ በትኩረት መስረት እንደሚገባ የሀድያ ዞን ምክር ቤት አባላት አሳሰቡ

የሀዲያ ዞን ምክር ቤት ምክትል አፈጉባኤ ወ/ሮ አለምነሽ ክፍሌ አስቸኳይ ጉባኤው መንግስት በ2018 በጀት ዓመት ለመንግሥት ሰራተኞች ባደረገው የደመወዝ ማሻሻያን ተከትሎ በታወጀው ተጨማሪ በጀት ዙሪያ መምከሩን ገልጿል።

ከመንግሥት የሚወርድ በጀትም ይሁን ከአከባቢው የሚሰበሰበው ገቢ በምክር ቤት ቀርቦ በሚያገኘው ዕውቅና መሠረት በስራ ላይ እንደሚውል ያመላከቱት ምክትል አፈጉባኤዋ፥ ምክር ቤቱ በተሰጠው ስልጣን መሰረት ያጸደቀውን በጀት ለታለመለት ዓለማ እንድውል የበኩሉን ክትትል ማድረግ ተገቢ መሆኑን አሳስበዋል።

ምክር ቤቱ በበጀት ዓመቱ ባደረገው ክትትል አበረታች ውጤት መመዝገቡን ጠቁመው፥ በቀጣይም ይህንን አጠናክሮ እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።

በዚህም የዞኑ ምክር ቤት የኢኮኖሚ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ሳሙኤል ዘመድኩን የ2018 በጀት አመት 10 ቢሊዮን 324 ሚሊዮን 740ሺህ 232 ብር በጀት ከክልል መውረዱን ጠቁመው፥ ተጨማሪ የ2 ቢሊዮን 853ሚሊዮን 405ሺህ 252 ነጥብ 24 ብር በጀት መታወጁን አስረድተዋል።

ይህም በጠቅላላ 13ቢሊዮን 178ሚሊን 145ሺህ 484 ነጥብ 24 ብር በጀት መሆኑን ለምክር ቤቱ የቀረበ ሲሆን፥ በጠቅላላ በጀት ዙሪያ የዞኑ ፋይናንስ ኃላፊ አቶ ሙሉጌታ ዱናሞ በኩል ዝርዝር ማብራሪያ ተሰጥቷል።

ከመንግሥት የሚመደቡ በጀቶች ለታለመላቸው ዓላማ እንዲውሉ በትኩረት መስራት እንደሚገባም ነው የምክር ቤቱ አባላት ያሳሰቡት።

አባለቱም የቀረበለትን የ2018 በጀት ዓመት የተጨማሪ የ2ቢሊዮን 853ሚሊዮን 405 ሺህ ብር 252 ነጥብ 24 ብር በጀት ተቀብለው በሙሉ ድምፅ አጽድቋል።

ዘጋቢ፡ ኤልያስ ኤርሶ – ከሆሳዕና ጣቢያችን