በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወጣቶች የማጠቃለያ መድረክ እየተካሄደ ነው

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወጣቶች የማጠቃለያ መድረክ እየተካሄደ ነው

ሀዋሳ፡ ሰኔ 14/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል “ሀገሬን እገነባለሁ፤ ኃላፊነቴን እወጣለሁ” በሚል መሪ ቃል የወጣቶች የማጠቃለያ መድረክ በወላይታ ሶዶ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል፡፡

መድረኩ የብልጽግና ፓርቲ ወጣቶች ክንፍ ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በመላው ሀገሪቱ ሲያካሂድ የቆየው የወጣቶች ዉይይት የማጠቃለያ መድረክ አካል እንደሆነ ተገልጿል።

በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የዲላ ክላስተር አስባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር)፤ ወጣቶች ክህሎታቸውን በመለየት የራሳቸውን ስራ መፍጠር ላይ በትኩረት እንዲሰሩ አስገንዝበዋል።

ክልሉ የ32 ብሔሮችና ብሄረሰቦች መኖሪያ መሆኑን ተገንዝቦ አብሮነትን ማጠናከር እንዲሁም ከሃሳብ እስከ ተግባር ያለውን ተሳትፎ ማጠናከር ወሳኝ ነዉ ብለዋል።

የብልጽግና ፓርቲ ወጣቶች ክንፍ ስራ አስፈፃሚ አባልና የወጣቶች ክንፍ ጽህፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ ወጣት ገዛኸኝ አንዳርጌ፤ ብልጽግና ለወጣቶች ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል ብለዋል።

ብልጽግና ያለ ወጣቶች ተሳትፎ ሁለንተናዊ ብልጽግናን ማረጋገጥ አይቻልም ብሎ በማመን በቅርቡ የወጣቱን ሚና በሚያሳይ መልኩ የስያሜ ለዉጥ ማድረጉንም ጠቅሰዋል።

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ የወጣቶች ክንፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ወጣት ሚካኤል ዋዳ፤ ብልጽግና ወጣቶች የሀገር ተረካቢ ብቻ ሳይሆኑ የሀገር ባለቤቶች ናቸው ብሎ እየሠራ እንደሚገኝ ገልፀዋል።

ክልሉን የሰላም ተምሳሌት በማድረግ ረገድ ወጣቶች ከፍተኛ ሚና እንዳለቸው ገልፀው፤ ለዚህም በክልሉ 47 ሺ 582 ወጣቶች በሰላም ክበባት ታቅፈዉ እየሰሩ እንደሚገኙ ጠቁመዋል።

ዘጋቢ፡ በቀለች ጌቾ – ከዋካ ጣቢያችን