የሴቶች ንግድና ኤክስፖ ሊካሄድ መሆኑ ተገለጸ

የሴቶች ንግድና ኤክስፖ ሊካሄድ መሆኑ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ግንቦት 30/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሴቶች ንግድና ኤክስፖ በቀጣዩ ሳምንት በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ።

የኢፌዴሪ ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዲኤታ ወ/ሮ አለሚቱ ኡሙድ እንደገለጹት “Business women Expo2023” በሚል ስያሜ ሊካሄድ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በዓይነቱ ልዩ የሆነ ኤክስፖ በተለያዩ የንግድ ዘርፎች የተሰማሩ ሴት ስራ ፈጣሪዎች፣ አምራቾች እና የንግድ ተቋም መሪዎች ምርትና አገልግሎቶቻቸውን ከ35 ሺህ በላይ ለሆኑ ጎብኝዎች ይሸጣሉ፣ ያስታዋውቃሉ ብለዋል።

በማምረቻ ኢንደስትሪ፣ በሆቴልና ቱሪዝም፣ በግብርና፣ በትምህርት፣ በጤና፣ በሪል ስቴትና በሌሎችም መስክ በሴቶች ባለቤትነት የተያዙና የሚመሩ ከ100 በላይ ድርጅቶች በኤክስፖ ይሳተፋሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ምርት ከመሸጥ ከማስተዋወቅ ባለፈ በፓናል ውይይቶች፣ በስልጠናዎችና ከባለድርሻ አካለት ጋር የተሻለ ግንኙነት በመፍጠር በዘርፉ የተሰማሩ ሴቶች የሚያጋጥሟቸውን ችግሮች ለመቅረፍና የኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሻሻል የሚያስችል የመስፈንጠሪያ መድረክ እንደሚሆንም ሚኒስትር ዲኤታዋ ተናግረዋል።

የንግድ ኤክስፖው ከሰኔ 7 ቀን 2015ዓ/ም ጀምሮ እስከ ሰኔ 9 ቀን 2015 ዓ/ ም በስካይላይት ሆቴል ለሦስት ተከታታይ ቀናት የሚቆይ ሲሆን የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ከማሌሳ ኤቨንት ጋር በመተባበር የሚያዘጋጀው ይሆናል።

በጉዳዩ ዙሪያም የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴርን ጨምሮ የማሌሳ ኤቨንት በጋራ በመሆን መግለጫ ሰጥተዋል።

ዘጋቢ፡ ጌታሁን አንጭሶ