በክልሉ እየተስተዋለ ያለው ህገ-ወጥ የህጻናት የጉልበት ብዝበዛና ፍልሰት ዘርፈ ብዙ ችግር እያስከተለ ነው -አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር)

በክልሉ እየተስተዋለ ያለው ህገ-ወጥ የህጻናት የጉልበት ብዝበዛና ፍልሰት ዘርፈ ብዙ ችግር እያስከተለ ነው -አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር)

የህፃናት ጉልበት ብዝበዛ ገፅታና ተጋላጭነት ላይ የተደረገ ክልላዊ የዳሰሳ ጥናት ውጤት ላይ ያተኮረ ምክክር በአርባ ምንጭ ከተማ ተካሂዷል።

በምክክር መድረኩ ላይ የተገኙት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት ም/ርዕሰ መስተዳድርና ስራ እድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ልማት ቢሮ ኃላፊ አበበየሁ ታደሰ (ዶ/ር) እንደተናገሩት በክልሉ በህፃናት ላይ እየደረሰ ያለው ህገ-ወጥ የጉልበት ብዝበዛ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ የሚገኝ በመሆኑ ባለ ድርሻ አካላት የተጣለባቸውን ኃላፊነት በአግባቡ ሊወጡ ይገባል።

በክልሉ እየተስተዋለ ያለው ህገ – ወጥ የህጻናት የጉልበት ብዝበዛና ፍልሰት የህፃናትን የመማር እድላቸውን በመንፈግ ለተለያዩ ማህበራዊ ችግሮች እየዳረጓቸው ስለመሆኑ የተናገሩት ም/ርዕሰ መስተዳደሩ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ማህበራዊ ተቋማት ላይ በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባም አሳስበዋል።

ዶ/ር አበባየሁ አያይዘውም የችግሩን አሳሳቢነትን በጊዜ ለመግታት የፍትህ ተቋማት በህ-ገወጥ የህፃናት ዝውውር ላይ የሚሳተፉ አካላት ላይ አስተማሪ የህግ ርምጃ በመውሰድ የድርሻቸውን ሊወጡ ይገባልም ብለዋል።

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በሚገኙ ኢንዱስትሪዎች ውስጥ ሳይቀር ህፃናት ጉልበታቸው እየተበዘበዘ መሆኑ ታውቆ በዘርፉ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ርብርብ ማድረግ ይገባልም ብለዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት ሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሰብስቤ ቡናቤ በበኩላቸው በክልሉ የሚስተዋለውን ህገወጥ የህጻናት ጉልበት ብዝበዛና ዝውውርን ለመግታት ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰው ለዚህም ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ስለ መሆኑም አመላክተዋል።

ዘጋቢ: በኃይሉ ሙሉጌታ