ሀዋሳ፡ ግንቦት 21/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የአርብቶ አደሩ ኑሮ የሚያሻሽሉና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአኗኗር ዘይቤ ለመፍጠር እየሠራ መሆኑን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አከባቢ ልማት ቢሮ ገለፀ።
ቢሮው በሥሩ የሚገኙ የተጠሪ ፕሮጀክቶች የ2017 በጀት አመት የ9 ወር የሥራ አፈፃፀምን ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በዲመካ ከተማ ገምግሟል።
በመድረኩ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማሊኮ ፕሮጀክቶች በመንግስት ደረጃ ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቁ በርካታ ሥራዎችን በማከናወናቸው አመስግነዋል።
ፕሮጀክቶች የሚተገብሯቸውን ሥራዎች በግልፀኝነት ሊያከናውኑ እንደሚገባም አስተዳዳሪው አሳስበው፥ የተጀመሩ ሥራዎችንም በባለቤትነት ተቀናጅተው እንደሚሠሩ ገልፀዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አከባቢ ልማት ቢሮ ልዩ ድጋፍ መሠረተ ልማት ማስተባበሪያ ዘርፍ ኃላፊ አቶ አይዴ ሎሞዶ ቢሮው የሕብረተሰቡ ተጠቃሚነትን በማረጋገጥ ምርትና ምርታማነትን በእንስሳት እና በግብርናው ዘርፍ ለማሳደግ በቴክኖሎጂ በመታገዘ አገልግሎት መስጠቱን ተናግረዋል።
ሕብረተሰቡን ተጠቃሚ ከሚያደረጉ ማህበራዊ ተቋማት የትምህርት ቤቶችና ጤና ጣቢያዎች ግንባታ መጠናከሩን አቶ አይዴ አክለው፥ የቢሮው ክትትልና ድጋፍ ማዕቀፍ ሥርዓትንም አስረድተዋል።
በፕሮጀክቶች የተከናወኑ ሥራዎችን ለታዳሚው ካቀረቡት መካከል የቆላማ አከባቢ ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት አስተባባሪ አቶ ሚሊዮን ተክሌ በበኩላቸው፥ የአርብቶ አደሩን ኑሮ የሚያሻሽሉና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአኗኗር ዘይቤ ለመፍጠር ከማህበረሰቡ ጋር በመሆን በርካታ ሥራዎች መከወኑን አስረድተዋል።
በምክክር መድረኩ ከተሳተፉ ባለድርሻ አካላት መካከል የሐመር ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሣሙኤል ጋርሾ እና የኧሌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አርሻሌ አርካሌ በጋራ እንደገለፁት በፕሮጀክቶች የተከናወኑ ሥራዎች የማህበረሰቡን ኑሮ ለመቀየር ተጨማሪ አቅም መፍጠሩን አስረድተው ቀሪ ሥራዎችም ውጤታማ እንዲሆኑ የድርሻቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል።
ዘጋቢ፡ ተመስገን አሰፋ – ከጂንካ ጣቢያችን

More Stories
በ6 ወራት ውስጥ ሊመዘበር የነበረ ከ156 ሚሊየን 560ሺህ ብር በላይ ማዳን መቻሉ ተገለጸ
የጉራጌ ክትፎ ባህልና እውቀትን በዩኒስኮ የሰው ልጆች ወካይ የማይዳሰስ ቅርስነት ለማስመዝገብ እየተሰራ እንደሚገኝ የኢፌዲሪ ቅርስ ባለስልጣን ገለፀ
በክልሉ ያሉ ብሔረሰቦችን ባህል ወደፊት በማውጣት የአካባቢውን ሰላምና ልማት ለማስቀጠል በትኩረት መስራት እንደሚገባ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳደር ኢንጅነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) ተናገሩ