በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች በቋሚነት የሚደገፉበት ስራ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የቡርጂ ዞን አስተዳደር አስታወቀ

የቡርጂ ዞን አስተዳደር፣ የዞኑ ሴቶችና ህጻናት ዩኒት፣ የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ዩኒት እና የወጣቶች ክንፍ በሶያማ ከተማ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች የማዕድ ማጋራት ስነ-ስርዓት አከናውነዋል።

የቡርጂ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳኜ ህዶ በስነ-ስርዓቱ ላይ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፤ ድጋፍ የተደረገው በተለያዩ መስሪያ ቤቶች እንደሆነና ወጣቶች ማህበረሰቡን በማስተባበር ያደረጉት በመሆኑ ትልቁን ድርሻ ይወስዳሉ ብለዋል።

ለአቅመ ደካሞች በበዓል ወቅት ብቻ ሳይሆን በሌሎች ጊዜያትም ድጋፉ ተጠናክሮ ይቀጥላል ያሉት ዋና አስተዳዳሪው፤ በቀጣይ በቋሚነት የሚደገፉበትና ስራ የሚያገኙበት አግባብ ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

የቡርጂ ዞን ሴቶች ክንፍ ኃላፊ ወ/ሮ ማሪያም ሲሳይ፤ የተደረገው ድጋፍ ከጎናችሁ መሆናችንን ማሳያ ነው በማለት ይህም አንድነት እና አብሮነትን እንደሚያጠናክር አስረድተዋል።

በተደረገላቸው ድጋፍ መደሰታቸውን የገለጹት ወ/ሮ ወለተኪዳን ገ/እግዚአብሔር እና ወ/ሮ ታፈሰች ታደሰ፤ መንግስትና ህዝብ ከጎናቸው እንደሆኑ በማሳየታቸው አመስግነዋል።

አቶ ወየሳ ማሞ የሶያማ ከተማ ነዋሪ ሲሆኑ ከዚህ በፊት በርካታ ድጋፎች ሲደረጉላቸው መቆየቱን በማንሳት ለህክምና እንዲሁም በቋሚነት ስራ እንዲሰሩ የተመቻቸላቸው መሆኑን ተናግረዋል።

ዘጋቢ: አሀዱ አሸናፊ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን