የትምህርት አጀንዳ “የሁሉም ልማት በኩር አጀንዳ ነው” ሲሉ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ ገለፁ

ለትምህርት ልማት ጥራት የተሰጠው ትኩረት ለውጥ እያስመዘገበ እንደሚገኝ ያብራሩት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ በየመድረኮቹ የሚተላለፉና ውሳኔ የሚተላልፍባቸው መልዕክቶች ለዘርፉ ውጤት ትልቅ አቅም እየፈጠረ ነው ብለዋል።

የትምህርት ለትውልድ ዋና መልዕክት ትምህርት ቤቶችን ማሳደግ፣ ማስዋብና ለተማሪዎች ማራኪ ማድረግ ዘርፉ ቀጣይነት ያለው ውጤት እንዲያስመዘግብ ትኩረት መስጠት ነው ሲሉም ርዕሰ መስተዳድሩ መልዕክት አስተላልፈዋል።

መላው ህዝብ ለዘርፉ የጀመረውን ድጋፍ አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም አሳስበዋል።

በመድረኩ የተገኙ አመራሮችና የሙያው ባለቤት የሆኑ የትምህርት ልማት ዘርፍ አመራሮችና ባለሙያዎች የተጣለባቸውን ሀላፊነት በትጋት እንዲወጡም አቶ ጥላሁን አሳስበዋል።

ጉባኤው ባለፉት ጊዜያት የተከናወኑ ተግባራት የሚገመገሙበት፣ በድክመት የተመዘገቡትን በመለየት በቁጭት ለቀጣይ ዕቅድ የሚከለስበት መሆን አለበት ብለዋል።

የአንድን ሀገር ሁለንተናዊ ለውጥ ለማረጋገጥ ትምህርት ዓይነተኛ ሚና ይጫወታል ያሉት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ትምህርት ቢሮ ሀላፊ ወ/ሮ ፀሐይ ወራሳ፤ ብቁና ተወዳዳሪ ዜጋን ለመፍጠር ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ይገኛል ብለዋል።

ከትምህርት ተደራሽነት አኳያ ሰፊ ሥራ የተሠራ ቢሆንም ከጥራት አንፃር ሰፊ ክፍተት ያለበት በመሆኑ ችግሩ ተለይቶ ከዘርፉ አመራሮችና ባለሙያዎች እንዲሁም ከመላው ህዝብ ጋር በመቀናጀት እየተሠራ እንዳለም ገልፀዋል ወ/ሮ ፀሐይ።

የኣሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብርሃም አታ፤ እንግዶችን በእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ተቀብለው ትምህርት የሁሉም ልማት መሠረት ነው ብለዋል።

በዕውቀትና በክህሎት የተሻለ ዜጋን ለመፍጠር ዘርፉን መደገፍ፣ በቁርጠኝነት መሥራትና ቀጣይነት ያለው ውጤት ማስመዝገብ ይጠበቃል ተብሏል።

በመድረኩ የክልሉ ትምህርት ቢሮ የዘጠኝ ወራት ዕቅድ አፈፃፀም እየቀረበ ነው።

ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ጣቢያችን