የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የህብረተሰቡን ችግር በሚፈቱ ጉዳዮች ዙሪያ የተጀመሩ የጥናትና ምርምር ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ተጠቆመ

የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የህብረተሰቡን ችግር በሚፈቱ ጉዳዮች ዙሪያ የተጀመሩ የጥናትና ምርምር ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ተጠቆመ

11ኛው “ምርምር ለልማት” ሀገር አቀፍ ዐውደ ጥናት በአርባምንጭ ዩኒቪርሲቲ ተካሂዷል።

የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ ምርምርና ትብብር ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ተክሉ ወጋየሁ በዩኒቨርሲቲው በተካሄደው 11ኛው ምርምር ሀገር አቀፍ ዐውደ ጥናት ስምፖዚየም ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት፤ በዩኒቨርሲቲው በዘላቂነት የህብረተሰቡን ችግር በሚፈቱ ጉዳዮች ዙሪያ የተጠኑ የተለያዩ የምርምርና ጥናት ስራዎች መሰራታቸውን አብራርተዋል።

የተለያዩ የምርምር ፅንሰ ሀሳቦችን በማቀናጀት በሀገሪቱ እየተስተዋለ ያለውን የትምህርት ስብራትን ለመጠገን በሚያስችሉና የተለያዩ የህብረተሰቡ ችግር ፈቺ በሆኑ ጉዳዮች የምርምና ጥናት ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አመላክተዋል።

የቀድሞ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንትና የኢትዮጵያ የኢኮኖሚክስ ባለሙያዎች ማህበር ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር ጣሰው ወልደሀና በበኩላቸው፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በጥናትና ምርምር የተደገፉ አዳዲስ ሀሳቦችን በማፍለቅ የፖሊሲና ቴክኖሎጂ ፈጠራ ስራዎችን አጠናክረው መስራት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።

በሀገሪቱ ዩኒቨርሲቲዎች ራስ ገዝ እንዲሆኑ የማድረግ ስራዎች መጀመራቸውን የገለፁት ፕሮፌሰር ጣሰው፤ ይህ ደግሞ የትምርህት ጥራትን ለማስጠበቅ የጎላ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል።

የአርባምንጭ ዩኒቪርሲቲ የምርምር ጉዳዮች ዳይሬክተር ዶ/ር ተስፋዬ ሐብተ ማሪያም፤ ዩኒቨርሲቲው በተለያዩ ችግር ፈቺ ጉዳዮች ዙሪያ ምርምርና ጥናት በማድረግ ተጨባጭ ውጤቶችን ማስመዝገብ መቻሉን ገልፀው ይህም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቅሰዋል።

ዘጋቢ፡ እንጃ ገልሲሞ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን