የመተጋገዝና የመተሳሰብ ወርቃማ እሴታችንን የበለጠ በማጎልበት በጋራ የመልማት ተስፋ እውን እንዲሆን የወጣቱ ሚና ከፍተኛ ስለመሆኑ በሀዲያ ዞን የጃጁራ ከተማ አስተዳደር ገለፀ

በከተማው የሚገኘው የ”መቴያ ማህበር” በደቡብ አፍሪካ ከተመሰረተው የቅንልቦች ማህበር ጋር በመተባበር ለአቅመ ደካማ ዜጎች የምግብ ቁሳቁስ ድጋፍ አድርጓል።

በድጋፍ አሰጣጡ ወቅት የተገኙት የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ አቶ ለይኩን ሱልዶሎ እንደተናገሩት፤ በአካባቢው ለሚኖሩ አቅመ ደካሞችና አረጋዊያን የተደረገው ድጋፍ ከመልካምነት የመነጨ በጎ ተግባር ነው።

በከተማው በተለያዩ በጎ ፈቃድ ተግባራት ላይ የሚሳተፉ የወጣቶች ማህበራት በስራ የሚገለፅ አስታዋሽ ያጡ አረጋዊያንና አቅመ ደካሞችን በመርዳት እጅግ የሚያስመሰግን ተግባራትን እያከናወኑ መሆናቸውን አቶ ለይኩን ገልፀዋል።

በማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን የስራ እንቅስቃሴ ውጤታማ የተቀናጀ ተግባር እየተከናወነ እንደሚገኝ የሚገልፁት ከንቲባው፤ ከራስ ይልቅ ለሌሎች ቅድሚያ የሚሰጥ ወጣት ትውልድ እየተፈጠረ እንዳለ አንስተዋል።

ወጣቶች በአካባቢያቸው ልማት ንቁ ተሳትፎ በማድረግ የበለፀገች የጋራ ሀገር ለመገንባት ሁሉአቀፍ አመለካከትና መከባበርን መላበስ እንዳለባቸው አሳስበዋል።

ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ በተለያዩ በጎ ተግባራት ላይ በመሳተፍ የበኩላቸውን ድርሻ እየተወጡ እንደሚገኙ የሚናገሩት የመቴያ ማህበር ወጣት አባላት፤ በደቡብ አፍሪካ ከሚገኘው ቅንልቦች ማህበር ጋር በመተባበር ለአቅመ ደካማ አረጋዊያን ምግብ ነክ ድጋፍ ማድረጋቸውን ጠቁመዋል።

በቀጣይ ጊዜያትም ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት በተጠናከረ መልኩ መሰል ተግባራትን ለማከናወን ሰፊ ዕቅድ እንዳላቸው ወጣቶቹ ገልፀዋል።

ወ/ሮ አዳነች ሊሞሬና አቶ ዮሐንስ ጫፋሞ ድጋፍ ከተደረገላቸው አቅም ደካሞች መካከል ሲሆኑ በወጣቶቹ የተሰጣቸው የምግብ ቁሳቁስ በሚያስፈልጋቸው ወሳኝ ጊዜ የቀረበላቸው መሆኑን ጠቁመው፤ እንደዚህ ዓይነት መሰል በጎ ተግባራት በሌሎች አካላትም ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው አስታውቀዋል።

ዘጋቢ: ዳኜ አየለ – ከሆሳዕና ጣቢያችን