በደቡብ ኦሞ ዞን ሐመር ወረዳ በሚገኙ የሐመር እና ኤርቦሬ ማህበረሰቦች መካከል ዘላቂ ሠላምን ለማስፈን የባህላዊ እርቅና ደንብ ስርአት በወረዳው አሲለ ቀበሌ ተከናውኗል፡፡
የእርቅ ስነ-ስርአቱ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የሐመር ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሳሙኤል ገርሾ እንደገለጹት፤ የዛሬው ባህላዊ ኩነት ያስፈለገው በሁለቱ ማህበረሰቦች መካከል የነበረውን አለመግባባት በሰላማዊ መንገድ ለመፍታትና ፊርማ በማኖር ባህላዊ የደንብ ስርአት በማከናወን ለማጽደቅ ነው።
በዚህም መሠረት የሁለቱ ማህበረሰቦች የሀገር ሽማግሌዎችና የጎሳ መሪዎች ባህላዊ ምርቃት በማድረግ የፊርማ ሰነዱ በዞኑ ሰላምና ጸጥታ መመምሪያ ተወካይ በአቶ ተስፋዬ አርባ ተነቦና ተተርጉሞ ፊርማቸውን የማኖርና ባህላዊ ስነ-ስርዓት አከናውነዋል።
የደቡብ ኦሞ ዞን ሰላምና ጸጥታ ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ ጎላ ጎዳቦ በበኩላቸው፤ በማህበረሰቡ መካከል በሳር ግጦሽና እርሻ መሬት በመሳሰሉት የሚፈጠሩ አለመግባባቶችን በባህላዊ እርቅ ስርአት መፍታት ከቀድሞ ጀምሮ ሲከናወን የቆየና አሁንም ይህን ለትውልድ ማስተላለፉ ተግባር የባለድርሻ አካላት በሙሉ ሊሆን እንደሚገባ አሳስበዋል።
በስነ-ስርአቱ ላይ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የጎሳ መሪዎች፣ የወረዳና የዞን መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ተሳታፊ ሆነዋል።
የእርቅ ስነ-ስርአቱም ሰላማዊ በሆነ መልኩ መካሔዱ እንዳስደሰታቸው ያነጋገርናቸው የመድረኩ ተሳታፊ አካላት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
ዘጋቢ፡ ተመስገን ሰይፉ – ከጂንካ ጣቢያችን

More Stories
ዲግሪው “ወረቀት ብቻ ሳይሆን፣ የሀገር ተስፋና የትውልድ ኃላፊነት ነው” – አፈወርቅ ካሱ (ፕ/ር)
በክልሉ የተጀመሩ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ የድጋፍና ክትትል ስራ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የመጠጥ ውሃና ሳኒቴሽን ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ዶ/ር አስፋው ዲንጋሞ ገለጹ
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርናና ገጠር ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በሀላባ ቁሊቶ ከተማ የግብርና ስራዎችን ተመለከተ