የቲቢ በሽታን ለመቆጣጠር በቅንጅት መሠራት እንደሚገባ ተጠቆመ
ሀዋሳ: መጋቢት 14/2017 (ደሬቴድ) የቲቢ በሽታን ለመቆጣጠር በቅንጅት መሠራት እንደሚገባ የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።
በአርባ ምንጭ ሲከበር የቆየው 19ኛው አመታዊ የቲቢ በሽታ ምርምር ጉባኤና የ2017 ዓ.ም. የዓለም የቲቢ በሽታ ቀን በእግር ጉዞ ተጠናቋል።
በየማጠቃለያ መድረኩ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት በጤና ሚኒስቴር የበሽታ መከላከል እና መቆጣጠር መሪ ሥራ አስፈጻሚ ስራ ዶ/ር ህይወት ሰለሞን የሳንባ ነቀርሳ በአለም ላይ ከፍተኛ የጤና መታወክ እያስከተለ በመሆኑ ለመቆጣጠር በቅንጅት ሊሠራ ይገባል ብለዋል።
በኢትዮጵያ በበሽታው በየዓመቱ በርካታ ሰዎች እንደሚሞቱ ገልጸው በተለይም መድሀኒት የተላመደ ቲቢ እየተስፋፋ በመሆኑ የግንዛቤ ሥራ በተጠናከረ ሁኔታ እንዲሰራ ዶ/ር ሕይወት አሳስበዋል።
በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ትብብር ምክትል ፕሬዚዳንት ተክሉ ወጋየሁ (ዶ/ር) በበኩላቸው በሽታውን ለመከላከል በቂ አቅም ያለን በመሆኑ ከቲቢ ነጻ ሕብረተሰብ ለመፍጠር መሠራት እንዳለበት አሳስበዋል።
የቲቢ ቀን የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ እንዲያዘጋጅ ዕድል በመሰጠቱ ዶ/ር ተክሉ አመሥግነዋል።
በዘርፉ የተሻለ ውጤት ለማምጣት እየተሰሩ ያሉ ጥናቶችና ቅንጅታዊ አሰራሮችን በማጠናከር የቲቢ በሽታ የአለም ጤና ስጋት እንዳይሆን መስራት እንደሚገባ ተናግረዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ምክትል እና የፕሮግራሞች ኃላፊ አቶ መና መኩሪያ በበኩላቸው የቲቢ ሕሙማን ልየታ እና ሕክምና አገልግሎት በተገቢው ሁኔታ በመስጠት በክልሉ የተሻለ አፈጻጸም መመዝገቡን ገልጸው በሽታውን ይበልጥ ለመግታት አሁንም የግንዛቤ ሥራ ሊጠናከር ይገባል ብለዋል።
በመድረኩ ቲቢን ለመከላከል ብሎም አክሞ በማዳን ምሣሌ የሆኑ የጤና ባለሙያዎች እና ተመራማሪዎች ልምዳቸው ያካፈሉ ሲሆን የማበረታቻ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
ለሶስት ተከታታይ ቀናት ” በርግጥም ቲቢን መግታት እንችላለን፤ ቃል በተግባር ሐብት ለውጤት ” በሚል መሪ ቃል ሲከበር የቆየው የዓለም የቲቢ ቀን በእግር ጉዞ እና በተለያዩ የግንዛቤ ማስጨበጫ ተግባራት ተከብሮ ውሏል።
ዘጋቢ: ወ/ገብርኤል ላቀው – ከአርባ ምንጭ ጣቢያችን

More Stories
በክልሉ የሚገኙ ነዋሪዎችን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል ሥራ በትኩረት እየተሠራ እንደሚገኝ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) ገለጹ
የእናቶችንና ጨቅላ ህፃናትን ሞት ለመቀነስ በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ
የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርእሰ መስተዳደር (ዶ/ር ) እንዳሻው ጣሰው በተገኙበት በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ምርቃትና የመሰረተ ድንጋይ የማስቀመጥ ስነ-ስረዓት እየተካሄደ ይገኛል