አዲሱን የ “ኤርፖርት ሲቲ” ግንባታ በተያዘው በጀት ዓመት ለማስጀመር ዝግጅት መደረጉን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ገለጸ

ፕሮጀክቱ በአጠቃላይ 5 ቢሊየን ዶላር በጀት እንደተያዘለትና በአምስት ዓመታት ውስጥ ተገንብቶ እንደሚጠናቀቅ ተገልጿል፡፡

በኦሮሚያ ክልል ከቢሾፍቱ ከተማ ጥቂት ወጣ ባለ ሥፍራ ላይ እንደሚገነባ የተገለጸው ይህ ፕሮጀክት÷ ዘመናዊ ሆቴሎች፣ ከቀረጥ ነጻ የግብይት ሥፍራና የካርጎ ሎጂስቲክ ማዕከል ይኖረዋል ተብሏል።

አየር መንገዱ አሁን ላይ ግንባታውን ለማስጀመር ፈረንሳይ በሚገኝ አንድ ኩባንያ አማካኝነት ጥናት አካሄዶ ማጠናቀቁን አቶ መስፍን ለኢዜአ ተናግረዋል፡፡

የፕሮጀክቱን ግንባታ ለማስጀመር ከኦሮሚያ ክልል ጋር በቅርበት እየተሠራ መሆኑን ጠቁመው÷ የፕሮጀክቱን ዲዛይን ለሚሠሩ ኩባንያዎች ጨረታ እንደሚወጣ እና በተያዘው ዓመት የዝግጅት ሥራዎችን በማጠናቀቅ ወደ ግንባታ ይገባል ብለዋል፡፡

ፕሮጀክቱ እንደ አስፈላጊነቱ በሁለት ምዕራፍ ተከፍሎ ሊገነባ እንደሚችልም ጠቁመዋል።