የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ከመቀሌ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ባስጀመረው የእንስሳት ዝርያ ማሻሻያ ፕሮግራም ላይ ያተኮረ ውይይት መካሄድ ጀመረ
ከአካባቢው የቁም እንስሳት ሐብት አንጻር ተጠቃሚነቱ እዚህ ግባ የሚባል ባለመሆኑ ሁኔታውን ለመቀየር ነው ፕሮጀክቱ መተግበር የጀመረው።
በአሪና ደቡብ ኦሞ ዞኖች ያለው የቁም እንሰሳት ቁጥሩን የሚመጥን ምርታማነት ዕውን ለማድረግ ዘመናዊ የአመራረት ስርአት መዘርጋት ቁልፍ ተግባር መሆኑን በመጥቀስ፤ ለዚህም ዩኒቨርሲቲው የመቀሌ ዩኒቨርሲቲን ልምድ በመጋራት የተሻለ ስራ ለመስራት የተቀናጀ ፕሮጀክት ትግበራ ሂደት መጀመሩን የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ኩሴ ጉድሼ ገልጸዋል።
በዚህ ረገድም የሁለቱ ዞኖች አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ተሳታፊ እንዲሆኑ መደረጉንም አስረድተዋል።
የጂንካ ዩኒቨርሲቲ የአስተዳደርና ልማት ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር አለሙ አይላቴ፤ በሁለቱ ዩኒቨርሲቲዎች የተጀመረው ፕሮጀክት ዓለማ፣ ግብና አተገባበርን ያስገነዘቡበትን የፕሮጀክት ሃሳብ አቅርበዋል።
አጠቃላይ የሀገሪቱ የእንስሳት ሃብትንና ተጠቃሚነት ከአለምአቀፍ ተጨባጭ ሁኔታ አንጻር ለውይይት ግብዓት በሚሆን መልኩ ጥናታዊ ጽሁፍ ያቀረቡት ደግሞ ከመቀሌ ዩኒቨርሲቲ የተገኙት ዶ/ር በሪሁ ገ/ኪዳን ናቸው።
በዩኒቨርሲቲያቸው የተተገበሩ ስኬታማ የእንስሳት ሀብት ልማት ስራዎችን በማሳያነት በማቅረብ፤ የእንስሳት ዝርያ በማሻሻል ውጤት ለማምጣት ሊተኮሩ በሚገባቸው ጉዳዮች ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
የአሪ ዞን አስተዳዳሪ አቶ አብርሃም አታ የዞኖቹን ባለድርሻ አካላት ያሳተፈ መድረክ መፈጠሩ ማህበረሰቡን ከሀብቱ ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል ጅማሬ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለትግበራው የሚጠበቅባቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል።
ሁለቱ ዩኒቨርሲቲዎች በቀጣይ ቅንጅታዊ ስራዎቻቸው የዘርፉን ችግር ለማቃለል ጥረት እንደሚያደርጉ አስታውቀዋል።
ዘጋቢ: ዳኜ ጥላሁን – ከጂንካ ጣቢያችን

More Stories
ህብር ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ የምርጫ ማኒፌስቶ፣ የዕጩ ማስተዋወቂያ እንዲሁም የምርጫ ቅስቀሳ ፕሮግራም በጎፋ ዞን ሳውላ ከተማ አካሄደ
ኦርቢስ ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ጥራት ያለው የአይን ህክምና በሀገሪቱ ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት እየሰራ መሆኑ ተገለፀ
ብልጽግና ፓርቲ የማህበረሰቡ ችግር የሚቀርፉ ፕሮጀክቶችን ገንብቶ በማጠናቀቅ በውጤታማነት ለአገልግሎት እያበቃ ነው – ዶ/ር መሀመድ ኑርዬ