ሀዋሳ፡ ጥቅምት 20/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የወሳኝ ኩነት ምዝገባ ለሀገራዊ ዕድገት የሚኖረው ፋይዳ የጎላ በመሆኑ ተቋማት ትክክለኛ እና ጥራት ያላቸውን መረጃዎችን በማደራጀት የበኩላቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ ኤጀንሲ ጠየቀ።
ኤጀንሲው ወቅታዊ የልደትና የሞት ኩነቶች ምዝገባ አተገባበር ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር በአርባ ምንጭ ከተማ የምክክር መድረክ አካሂዷል።
ተቋማት የዜጎችን ልደትና ሞት ኩነቶች መረጃ በመመዝገብ እና በማደራጀት ለሀገራዊ ኢኮኖምያዊ፣ ማህበራዊ እና ፖለቲካዊ ፋይዳ የበኩላቸውን እንዲወጡ የክልሉ ወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሣሙኤል ፎላ ጠይቀዋል።
ባለ ድርሻ አካላት በተለይም ጤና፣ ትምህርት፣ ፐብሊክ ሰርቪ፣ ፍርድ ቤት፣ ሴቶች ህጻናት እና የሃይማኖት ተቋማት ዋነኛ ተዋናይ በመሆናቸው ለትክክለኛ መረጃ ጥንቅር አበክረው እንዲሠሩ ተጠይቋል።
ከባለድርሻ አካላት አንዱ የሆነው ጤና ቢሮ በጤና ጣቢያዎች እና ሆስፒታሎች የተጀመረው የልደት እና ሞት ምዝገባ ተግባር ተጠናክሮ እየተሠራ ስለመሆኑ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ የቢሮ ምክትል ሀላፊ እና የጤና ፕሮግራሞች ሀላፊ አቶ መና መኩሪያ ገልጸዋል።
የሃይማኖት ተቋማት የአባላትን ወቅታዊ የልደት ሞት እና ጋብቻ ምዝገባ ሽፋን ለማሣደግ ተጨባጭ መረጃዎችን ከማደረጀት አኳያ ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባ በምክክር መድረኩ ተብራርቷል።
በ2017 ዓ/ም የሦስት ወራት የወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ አፈጻጸም ስታይ አፈጻጸሙ ዝቅተኛ በመሆኑ በትኩረት እንዲሠራ ኤጀንሲው አሳስቧል።
ዘጋቢ፡ ወ/ገብርኤል ላቀው – ከአርባ ምንጭ ጣቢያችን

More Stories
የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ መንግሥት ወቅቱን የጠበቀና ጥራት ያለው ውሳኔ እንዲሰጥ የሚያስችል መሆኑን በኢትዮጵያ ስታትስቲክስ አገልግሎት የአርባምንጭ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ገለፀ
የጎርፍ መውረጃ ቦይ አለመሠራት በቤት ንብረታቸው ላይ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን በከምባታ ዞን የዳምቦያ ከተማ አስተዳደር የ02 ቀበሌ ነዋሪዎች ገለጹ
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት የፕላን መሰረተ ልማት እና የመንግስት ሀብት አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በአርባ ምንጭ ከተማ የ2018 በጀት አመት የመጀመሪያ ግማሽ አመት የተከናወኑ ተግባራትን የመስክ ምልከታ አደረገ