አጀንዳዎችን በማሰባሰብ የህዝቡ ጥያቄ በተገቢው እንዲመለስ የምክክሩ ሂደቱ የላቀ አስተዋፅኦ እንዳለው ተሳታፊዎች ገለፁ
ሀዋሳ፡ ጥቅምት 19/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) አጀንዳዎችን በማሰባሰብ የህዝቡ ጥያቄ በተገቢው እንዲመለስ የምክክሩ ሂደቱ የላቀ አስተዋፅኦ እንዳለው ተሳታፊዎች ገልፀዋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል እየተካሄደ ያለው የአጀንዳ አሰባሰብና ተወካይ መረጣ መቀጠሉን የምክክር ኮሚሽኑ የክልሎች፣ የሁለቱ ከተማ አስተዳደር እና ዲያስፖራ አስተባባሪ አስታውቀዋል።
የምክክር ሂደቱን አስመልክተው አስተያየት የሰጡን የጌዴኦ ዞን ተሳታፊ መምህር አስራት እሸቱ እና የጎፋ ዞን ተሳታፊ መቶ አለቃ ተፈሪ ጤናው እንደ ሀገር የሚስተዋሉ ችግሮችን ለይቶ በሰለጠነ መንገድ መወያየት እና መፍትሄ መፈለግ ይገባል ብለዋል።
መንግስትም የህዝቡን አጀንዳ በመቀበል የልማት እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን በተገቢው በመመለስ ግጭቶች እንዳይፈጠሩ በትኩረት ሊሰራ ይገባል ያሉት ተሳታፊዎቹ የተሻለችውን ኢትዮጵያ ለመገንባት ባህላዊ የግጭት አፈታት ስርአትን ማጎልበት እና ባህላዊ ሸንጎዎችን ማስፋፋት ይገባል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ምክክር ኮሚሽን የ7ቱ ክልሎች፣ የሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች እና የዲያስፖራ አስተባባሪ አቶ ረታ ጌራ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከ2 ሺህ በላይ ተሳታፊዎች የአጀንዳ አሰባሰብና የተወካይ መረጣ እያካሄዱ መሆኑን ጠቁመዋል።
በቀጣይ ቀናትም ተፅእኖ ፈጣሪ እና ታዋቂ ሰዎች እንዲሁም የመንግስት አካላት እና የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚመክሩበት እና አጀንዳ የሚመርጡ መሆኑን አስታውቀዋል።
በደቡብ ኢትዮጰያ የምክክር እና የአጀንዳ መረጣ ሂደት ያለምንም ችግር እየተካሄደ መሆኑን የገለፁት አቶ ረታ በክልሉ የሚደረገው ሂደት የተሳካ እንዲሆን የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርስቲ ላበረከው አስተዋፅኦ በኮሚሽኑ ስም አመስግነዋል።
በወላይታ ሶዶ ከተማ እየተደረገ ያለው የምክክ ሂደት በቀጣይ 3 ተከታታይ ቀናት እንደሚቀጥልም ተመላክቷል።
ዘጋቢ ፡ ገነት መኮንን – ከአርባምንጭ ጣቢያችን

More Stories
የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ መንግሥት ወቅቱን የጠበቀና ጥራት ያለው ውሳኔ እንዲሰጥ የሚያስችል መሆኑን በኢትዮጵያ ስታትስቲክስ አገልግሎት የአርባምንጭ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ገለፀ
የጎርፍ መውረጃ ቦይ አለመሠራት በቤት ንብረታቸው ላይ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን በከምባታ ዞን የዳምቦያ ከተማ አስተዳደር የ02 ቀበሌ ነዋሪዎች ገለጹ
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት የፕላን መሰረተ ልማት እና የመንግስት ሀብት አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በአርባ ምንጭ ከተማ የ2018 በጀት አመት የመጀመሪያ ግማሽ አመት የተከናወኑ ተግባራትን የመስክ ምልከታ አደረገ