ጥራቱን የጠበቀ የቡና ምርት አቅርቦትን በማስጠበቅ የሀገር ምጣኔ ሀብት ዕድገት ይበልጥ እንዲረጋገጥ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 29/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ጥራቱን የጠበቀ የቡና ምርት አቅርቦትን በማስጠበቅ የሀገር ምጣኔ ሀብት ዕድገት ይበልጥ እንዲረጋገጥ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን በኣሪ ዞን የደቡብ ኣሪ ወረዳ ቡናና ቅመማ ቅመም ልማት ጽህፈት ቤት አስታወቀ።

ምርታማነቱ በምርምር የተረጋገጠ ምርጥ የቡና ዘር ችግኝ ዝግጅትና ስርጭት እየተካሄደ መሆኑም ተገልጿል።

በዞኑ በደቡብ ኣሪ ወረዳ ከ9ሺ 800 ሄክታር በላይ መሬት በቡና ተክል የተሸፈነ መሆኑን የገለፁት የወረዳው ቡናና ቅመማ ቅመም ልማት ፅህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ታገል ደይጣቆ በ2017 በጀት ዓመት የተሻለ ጥራት ያለው የቡና ምርት እንዲኖር ሲሰራ ቆይቷል ብለዋል።

ሀላፊው አያይዘውም ጥራቱን የጠበቀ የቡና ምርት ለገበያ ማቅረብ እንዲቻል የተለያዩ ተግባራትን ከባለድርሻ አካላት ጋር እያከናወኑ እንደሚገኙም ገልጸዋል።

የወረዳው አርሶ አደሮች ቡናን በጥራት በማምረት የተሻለ ጥቅም እንዲያገኙ ምርጥ የቡና ዘር ለችግኝ ጣቢያዎች በማቅረብ ከ1 ሚሊዮን 500 ሺህ በላይ ችግኞችን በማዘጋጀት ማሰራጨት መቻሉም ተመላክቷል።

በቀበሌ ደረጃ አርሶ አደሮች ጥራቱን የጠበቀ ምርት ለገበያ እንዲያቀርቡ አስፈላጊ ቅድመ ዝግጅት እያደረጉ መሆናቸውን በወረዳው የመስክ ግብርና ባለሙያ አቶ ዳዊት በዙ ገልጸዋል።

በጥራቱ በገበያ ተወዳዳሪ የሆነ የቡና ምርት በማቅረብ ለአገር ምጣኔ ሀብት ዕድገት የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት የሚጠበቅባቸውን ሀላፊነት በተገቢው መወጣት እንደሚገባም ባለሙያው አስረድተዋል።

በየደረጃው በሚካሄድ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች ቡና አምራቹ ማህበረሰብ ለምርት ጥራት የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ እንደሚገኝም ተገልጿል።

በዞኑ የደቡብ ኣሪ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ግዛው ሀይሌ እንደገለፁት በወረዳው የቡና ምርት በስፋት ለገበያ እየደረሰ ስለሚገኝ ጥራቱን የጠበቀ የቡና ምርት አቅርቦትን ለማስፈን በቅንጅት እየተሰራ ይገኛል።

ዘጋቢ፡ ዳኜ ጥላሁን – ከጂንካ ጣቢያችን