ቢሮው በበጀት አመቱ በውሀ፣ መስኖና ማዕድን ልማት ስራዎች የተሻሉ ተግባራት ለማከናወን ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን አስታወቀ

በበጀት አመቱ በውሀ፣ መስኖና ማዕድን ልማት ስራዎች የተሻሉ ተግባራት ለማከናወን ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ውሀ፣ መስኖና ማዕድን ልማት ቢሮ አስታወቀ፡፡

ቢሮው ከተጠሪ ተቋማት ጋር በ2017 በጀት አመት የፈጻሚ ዝግጅት መድረክ አካሂዷል።

መድረኩን በንግግር የከፈቱት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ውሀ፣ መስኖና ማዕድን ልማት ቢሮ ሀላፊ አቶ ዳዊት ሀይሉ እንደገለጹት ክልሉ ከተመሰረተ አንድ አመት ማስቆጠሩና በዚህም በውሀ፣ መስኖና ማዕድን ልማት ስራዎች ላይ አመርቂ ውጤት ተመዝግቧል።

በ2016 በጀት አመት በርካታ ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን የገለጹት ሀላፊው በተያዘው በጀት አመትም እየተገነቡ ያሉ ፕሮጀክቶችን አገልግሎት መስጠት እንዲጀምሩ በትኩረት አየተሰራ ነው ብለዋል።

ከፈጻሚው አካላት ጋር በመሆን ባለፈው በጀት አመት የተሻለ ስራ መሰራቱና በተያዘው በጀት አመትም እነዚህን ተግባራት አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚያስፈልግ አቶ ዳዊት አመላክተዋል።

ለ2017 በጀት አመት በታቀዱ ተግባራት ላይ የጋራ መግባባት ላይ ለመድረስ መድረኩ መዘጋጀቱና የታቀዱትን ተግባራት ግብ ለማድረስ በየደረጃው ያሉ ፈጻሚ አካላት የድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል ብለዋል።

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ውሀ፣ መስኖና ማዕድን ልማት ቢሮ የእቅድ ክትትልና ድጋፍ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ እንዳልካቸው መኮነን እንደገለጹት ቢሮውና ተጠሪ ተቋማት በ2017 በጀት አመት 88 የንጹህ የመጠጥ ውሀ ፕሮጀክቶች፣ 10 የመስኖ ተቋማት፣ 329 አዲስና 200 የባዮጋዝ ጥገና እና 2 የሶላር ሚኒ ግራድ ወደ ስራ ለማስገባት ይሰራል ብለዋል።

በተያዘው በጀት አመት ግንባታቸው ተጀምረው ሳይጠናቀቁ ረጅም አመታት ያስቆጠሩ ነባር ፕሮጀክቶችን ቅድሚያ በመስጠት ለማጠናቀቅ እንደሚሰራ ጨምረው ገልጸዋል።

የመድረኩ ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየትም የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ተግባራትን በትብብር ለማከናወን ዝግጁ መሆናቸውን አብራርተዋል።

ባለፈው በጀት አመት የነበሩ ጥሩ ተሞክሮዎችን በማስቀጠልና ጉድለቶችን በማረም በተለይም የተጀመሩ ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ በትኩረት መስራት ያስፈልጋል ነው ያሉት።

በመጨረሻም ቢሮው ከተጠሪ ተቋማት ጋር የግብ ስምምነት ተፈራርሟል፡፡

ዘጋቢ፡ መላኪ ንማኒ – ከወልቂጤ ጣቢያችን