ካሜሮን ከአሰልጣኝ ሪጎበርት ሶንግ ጋር ተለያየች

ካሜሮን ከአሰልጣኝ ሪጎበርት ሶንግ ጋር ተለያየች

በ34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በጥሎ ማለፉ በናይጄሪያ ተረታ ከውድድሩ የተሰናበተችው ካሜሮን ከዋና አሰልጣኟ ሪጎበርት ሶንግ ጋር ተለያይታለች።

የአምስት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ ባለክብሯ የአሰልጣኙ ውል በትናንትናው ዕለት በመጠናቀቁ እና ውሉን ለማደስ ባለመፈለጓ ነው የተለያዩት።

የካሜሮን እግርኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት እና የቀድሞ የብሔራዊ ቡድኑ አጋር ሳሙኤል ኤቶ “እቅዳችን ባለመሳካቱ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው ውሉን ማራዘም አልፈለገም” በማለት ለፍራንስ 24 በአሰልጣኙ ስንብት ማብራሪያ ሰቷል።

የ47 ዓመቱ አሰልጣኝ ሪጎበርት ሶንግ እኤአ በ2022 በወርሐ የካቲት ቶኒ ኮንሴሣኦን በመተካት ነው የካሜሮን ብሔራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ የሆኑት።

አሰልጣኙ በሁለት ዓመት ቆይታው 23 ጨዋታዎችን መርቶ 6 አሸንፎ 26 በመቶ የማሸነፍ ንፃሬ አስመዝግቧል።

ዘጋቢ፡ ሙሉቀን ባሳ