በጤና ተቋማት የአሰራር ክፍተት በሚፈጥሩ አካላት ላይ አስተማሪ እርምጃ መውሰድ እንዲቻል የዘርፉ መዋቅሮች ድጋፍ ሊጠናከር ይገባል።

የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት አባላት በ6 ወር አፈፃፀም ግምገማ ላይ ላቀረቡት ጥያቄ የክልሉ ጤና ቢሮ ምላሽና ማብራሪያ ሰጥቷል።

በክልሉ ምክር ቤት በቀረበው የ2016 በጀት ዓመት የአስፈፃሚ አካላት በ6 ወር ሪፖርት ዙሪያ በጤናውም ዘርፍ አባላቱ መጠናከር እንዳለባቸውና መሻሻል አለባቸው ያሏቸውን ጥያቄዎችን ያቀረቡት ሲሆን የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ እብራሂም ተማም ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል።

በክልሉ የተከሰተውን የወባ ወረርሽኝ ለመከላከል የክልሉ መንግስት በርካታ ሥራዎችን የሠራ ቢሆንም ቅድመ በሽታ መከላከልና የተመደቡ በጀቶችን በአገባቡ ከመጠቀም ጋር በታችኛው መዋቅሮች ውስንነቶች መኖራቸውን ገልፀው በዘርፉ በትኩረት እንደሚሠራ ገልፀዋል።

የHIV ADS ቫይረስ ስርጭት በተለይ ትላልቅ ፕሮጀክቶች በሚሰሩበት አካባቢዎች እየበዛ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ እነዚህን ቦታዎች ልያታ በማድረግና ከተለያዩ አካላት ጋር በመቀናጀት የመከላከል እና ምርመራ ሥራ እየተሠራ ነው ብለዋል።

የወላድ እናቶችን ማቆያ በሁሉም መዋቅሮች ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ ሲሆን ቤቶችን በማደስና በጤና ተቋማት የወሊድ አገልግሎት ተደራሽነትን ለማሳደግ ተጠናክሮ ይሰራል ብለዋል።

የአምቡላንስ አገልግሎት ከእናቶችና ህፃናት ውጪ አመራሮች እየተጠቀሙ ያሉ ዞኖች እንዳሉም እንደተገመገመ አንስተው ቀጣይ ርምጃው አወሳሰድ እንደሚጠናከር ተናግረዋል።

በክልሉ ያደሩ የጤና መሰረተ ልማት ግንባታዎችን ከማስጀመር አኳያ በርካታ ሥራዎች እየተሰሩ ቢሆንም የማህበረሰቡ አካላት ዘርፉን መደገፍ እንዳለባቸውና በአንዳንድ አካባቢዎች ድጋፍ የተጀመረ መሆኑንም አቶ እብራሂም አብራርተዋል።

ከየማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህን አገለግሎት ጋር ተያይዞም በክልሉ ንቅናቄውን ቀድሞ በመጀመር 25% ከነበረው አሁን ላይ በተፈጠረው ንቅናቄ 35% መድረሱንና ቀጣይ የባለድርሻ አካላት ድጋፍ ቢጠናከር ዕቅዱን ማሳካት እንደሚቻልም ገልጸዋል።

ለጤና ተቋም የአመት በጀት ያልበጀቱ ወረዳዎችም እንዳሉ በመጠቆም በተዋረድ ያሉ አካላት ችግሩን ለመቅረፍ የበኩላቸውን እንዲደግፉ ጠይቀዋል፡፡

በጤና ተቋማት የአሰራር ክፍተት በሚፈጥሩ አካላት ላይ አስተማሪ እርምጃ ከመውሰድና ህገወጥ የመድኃኒት ዝውውርን ለማስቀረት ቢሯቸው በትኩረት እንደሚሰራም የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ እብራሂም ተማም ተናግረዋል።

በምክር ቤቱ ከተሳታፊዎች ለተነሱ ሀሳቦችና ጥያቄዎች የአስፈጻሚ ቢሮ ኃላፊዎች ቀጣይ መስራት ይበልጥ መስራት በሚያስችሉ ተግባራት ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል።

ዘጋቢ፡ ዮሐንስ መካሻ – ከዋካ ጣቢያችን