በክልሉ የተጀመሩ የንፁህ መጠጥ ውሀ ፕሮጀክቶች እንዲጠናቀቁ ቋሚ ኮሚቴው አሳሰበ

ሀዋሳ፡ ጥር 29/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በክልሉ የተጀመሩ የንፁህ መጠጥ ውሀ ፕሮጀክቶች እንዲጠናቀቁ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የግብርናና ገጠር ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ ።

በደቡብ ኢትዮጵያዊ ክልል በ15 ከተሞች የንፁህ መጠጥ ውሀ ግንባታ እንዲሁም በሶዶና አርባምንጭ ከተሞች የሳኒቴሽን ግንባታ እየተከናወነ እንደሚገኝ የክልሉ ውሀ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ጠቁሟል ።

በሪፖርቱ በግማሽ ዓመት ውስጥ የክልሉን ህዝብ የመጠጥ ውሀ ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸው በማዕድን ልየታ ፣ በጌጣጌጥ ማዕድናት ማምረት ላይ ለተሰማሩ ማህበራት የገበያ ትስስር መፈጠሩ ተገልጿል ።

በግማሽ ዓመት ውስጥ በመደበኛ፣ ካፒታል ፣በኤስዲጂ ፣ በአሃዳዊ ዋሽ ፣ ኮዋሽ ፣ በዩኒሴፍ እና በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት በክልሉ በሚገኙ የተለያዩ አከባቢዎች በገጠር 14 የውሀ ተቋማትን በከተማ ደግሞ 3 የውሀ ተቋማትን በመገንባት 41 ሺህ 440 ህዝብንን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ።

በአማራጭ ኢነርጂ ፣ በማዕድን ሀብት ጥናት ፣ የውሃ ተቋማት ዘለቄታዊ አገልግሎት እንዲሰጡ ከማድረግ ፣ የአደጋ ስጋት ዝግጁነት የቅድመ ዳሰሳ ጥናት ፣ ድጋፍና ክትትል ማድረግ መቻሉን በሪፓርቱ ቀርቧል ።

በክልሉ በገጠርና በከተማ የንፁህ መጠጥ ውሀ ሽፋን 52 በመቶ መድረሱን በሪፓርቱ ተመላክቷል ።

በቀረበው ሪፖርት ዙሪያ የማብራሪያ ጥያቄዎች ከቋሚ ኮሚቴው ተሰንዝሮ ከመድኩ ሰፊ ማብራሪያ ተሰጥቶበታል ።

በፕሮጀክቶች አፈፃፀም ላይ የውጪ ምንዛሬ ጫና እንደፈጠረ የጠቆሙት የክልሉ ውሀ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር አክሊሉ አዳኝ የሚገጥሙ ችግሮችን በቀጣይ ለመፍታት በቅንጅት እንደሚሰራ አብራርተዋል ።

የከተሞችን የውሀ አቅም እንዲያድግ ከግብረ ሰናይ ድርጅቶችና በህብረተሰቡ ተሳትፎ በዘላቂነት ለመፍታት ይሰራል ሲሉ ጠቁመዋል ።

የሶላር ቴክኖሎጂና የማዕድን ልማት እድገት በክልሉ እንደሚስተዋል ኢንጂነር አክሊሉ ጠቁመው ዋነኛ የቢሮው ችግር በጀት መሆኑንም አብራርተዋ ።

ችግሩን ለመቅረፍ በቀጣይ እንደሚሰራ ገልጸዋል ።

የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ የተከበሩ አቶ ጠንክር ጤንካ በቀጣይ የህብረተሰቡን የንፁህ መጠጥ ውሀ ፍላጎት ለማሟላት የተጀመሩ አበረታች ጥረቶች ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው ብለዋል ።

ዘጋቢ ፡ ተመኙህ ገረሱ- ከአርባምንጭ ጣቢያችን