ህብረተሰቡ አንፃራዊና ተገቢ የመንገድ መሰረተ ልማት እንዲያገኝ በቀጣይ በትኩረት እንደሚሰራ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መንገዶችና ትራንስፖርት ቢሮ አስታወቀ

የኢኮኖሚ መሰረት የሆነውን መንገድ በማልማት የህዝብ ለህዝብ ትስስርን ማጠናከር እንደሚያስፈልግ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ፕላን መሠረተ ልማትና የመንግስት ሀብት አስተዳደር ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ገልጿል።

ኮሚቴው የክልሉን መንገዶችና ትራንስፖርት ቢሮ የ2016 በጀት ዓመት የ6 ወራት ዕቅድ አፈፃፀም ገምግሟል።

የትራንስፖርት አገልግሎት ደህንነቱ የተጠበቀ እንዲሆን አዲስ መንጃ ፍቃድ አሳትሞ የማሰራጨት፣ ድንገተኛ የቴክኒክ ምርመራ የማድረግና ብቃት የማረጋገጥ፣ አለምአቀፍ የመንገድ ዳር ምልክቶችን የመትከል ተግባር በግማሽ በጀት ዓመቱ መፈፀሙን በቀረበው ሪፖርት ተጠቁሟል።

የመንገድ ደህንነት ግንዛቤ መፍጠር፣ ድንገተኛ የትራፊክ ቁጥጥር፣ የክረምት በጎ ፍቃደኞች ጋር በመተባበር የትራፊክ አደጋ የመቀነስ ተግባራት ተከናውነዋል።

የአሽከርካሪ ብቃትንና ችግርና የስነ -ምግባር ጉድለቶችን በመቅረፍ አገልግሎቱን ለማዘመን በልዩ ትኩረት እንደሚሰራ የክልሉ መንገዶችና ትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ዘብዲዮስ ኤካ ጠቁመዋል።

ህብረተሰቡ አንፃራዊ እና ተገቢ የመንገድ መሰረት ልማት እንዲያገኝና የተጀመሩትን ለማስጨረስ የተቋረጡ መንገዶችን ደግሞ በቀጣይ ለማስጀመር ትኩረት ተሰጥቶ ይሰራል።

የሚስተዋሉ የአቅም ውስንነቶችን ከክልሉ መንግስት ጋር በመነጋገር ለመፍታት ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ የጠቆሙት ኃላፊው ቋሚ ኮሚቴው ታች ድረስ ወርዶ ችግሮችን በመመልከቱና ለመፍትሔው በመስራቱ አመስግነዋል።

በቀረበው ሪፖርት ላይ ቋሚ ኮሚቴው የማብራሪያ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን ሰንዝሯል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ፕላን መሠረተ ልማትና የመንግስት ሀብት አስተዳደር ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ እንቁ ዮሀንስ እንደገለጹት ቋሚ ኮሚቴው ታች ወርዶ የመንገድ መሰረተ ልማቶችን መመልከቱን ጠቁመው በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮችን በመፍታት የህብረተሰቡን እሮሮ ማስቀረት ያሻል።

የኢኮኖሚ መሰረት የሆነውን መንገድ በማልማ የህዝብ ትስስርን ማሳደግ የህዝብን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንደሚያስፈልግም የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ አሳስበዋል።

ዘጋቢ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን