ሴቶችና ወጣቶች የሀገሪቱን መፃኢ ዕድል ብሩህ ለማድረግ ትልቅ ሚና እንዳላቸው ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው ገለፁ

ሀዋሳ፡ ጥር 29/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ወጣቶች የሀገሪቱን መፃኢ ዕድል ብሩህ ለማድረግ ትልቅ ሚና እንዳላቸው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው ገልጸዋል፡፡

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የብልፅግና ፓርቲ የሴቶች እና ወጣቶች ሊጎች የጋራ ማጠቃለያ መድረክ በሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ ነው።

በዚህ መድረክ ላይ የተገኙት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው እንደገለፁት ከታችኛው መዋቅር ጀምሮ በተካሄደው ውይይት ወደ አንድ ሚሊየን የሚጠጉ ሴቶችና ወጣቶች መሳተፋቸውን ተናግረዋል።

የመድረኩ ዓላማ ሴቶችና ወጣቶች ለሀገራቸው ሰላም መረጋገጥ፣ ለዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታና ለፍትሃዊነት መጎልበት አወንታዊ ሚና እንዲጫወቱ ነው ብለዋል።

በክልሉ ያሉ ወጣቶች ነጠላ ትርክቶች ታርመው ገዢና የጋራ ትርክቶች ቦታውን እንዲይዙ መስራት እንደሚገባም አሳስበዋል።

የሀገሪቱን መፃኢ ዕድል ብሩህ ለማድረግ የሴቶችና የወጣቶች ሚና ገንቢ መሆኑንም ጠቁመዋል።

በሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ ባለው የማጠቃለያ መድረክ ላይ ከአንድ ሺህ በላይ ተሳታፊዎች ተገኝተዋል።

ከመላው የክልሉ አካባቢዎች የተውጣጡ ሴቶች፣ ወጣቶች እና ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ።

ዘጋቢ፡ ጀማል የሱፍ