የአፈርና ውኃ ጥበቃ ስራ  የአካባቢን ስነ ምህዳር ከመቀየር አንጻር ጉልህ ሚና እንዳለው ተገለጸ

የአፈርና ውኃ ጥበቃ ስራ  የአካባቢን ስነ ምህዳር ከመቀየር አንጻር ጉልህ ሚና እንዳለው ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ጥር 28/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የአፈርና ውኃ ጥበቃ ስራ  የአካባቢን ስነ ምህዳር ከመቀየር አንጻር ጉልህ ሚና ያለው መሆኑን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሀዲያ ዞን ግብርና መምሪያ አስታወቀ።

የ2016 ዓ.ም የተቀናጀ የበጋ ግብርና ልማት ስራ የንቅናቄ ማብሰሪያ መርኃግብር በዞኑ አንሌሞ ወረዳ ተካሄዷል።

የሀዲያ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊና የመምሪያው ተወካይ አቶ ተሻለ ዮሐንስ እንደገለፁት የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ የአንድን አካባቢ ስነ ምህዳር ከመቀየር አንጻር ያለው ድርሻ ጉልህ መሆኑን አመላክተዋል።

እንደ ሀገር የተፋሰስ ልማት ስራ ከተጀመረ ወዲህ በርካታ የስነ ሕይወታዊ ገጽታ ለውጦችን ማየት ተችሏል ያሉት ኃላፊው፥ ባለፉት ጊዜያት በተከናወኑ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ስራዎች በዞኑ በርካታ ለውጦች መታየታቸውን አውስተዋል።

በዘንድሮው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ ከ78ሺ 6መቶ ሄክታር በላይ ማሳ በስነ አካላዊና  ስነ ሕይወታዊ ተግባራት ለማልማት ታቅዶ ወደ ተግባር የተገባበት መሆኑንና ለዚህም 3መቶ 11 ንዑስ ተፋሰሶችን የመለየት ስራ መሰራቱንም ገልፀዋል።

አቶ ተሻለ አክለውም በሁሉም አካባቢዎች አስፈላጊ ሁሉ ቅድመ ዝግጅት ቀድሞ የተደረገ  መሆኑን አመላክተዋል።

በዞኑ የአንሌሞ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ፀደቀ ግርማ ዞናዊ  የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ ማስጀመሪያ መርኃግብር በሚካሄድበት የ”ጉናሜ ተፋሰስ”ም ሆነ በወረዳው በሚገኙ ሌሎች አካባቢዎች የእንሰት ልማት ስራ ከምን ጊዜም በላይ ትኩረት የሚሰጥበት መሆኑን አመላክተዋል።

የእንሰት ልማት ስራ እንደ አካባቢው የህብረተሰቡን የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ አልፎ ገበያን በማረጋጋት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ በመጠቆም።

የሀዲያ ዞን ዋና አስተዳዳሪና የዕለቱ የክብር እንግዳ አቶ አብርሃም መጫ በበኩላቸው የመሬትን ለምነት ስንጠብቅ የሰው ልጅ የመኖር እድሉ እየሰፋ የሚሄድ ስለሆነ  መሬትን መንከባከብ የህልውና ጉዳይ ነው ብለዋል።

ስለሆነም  የአፈርና ውኃ ጥበቃ ስራ ዓመት ተጠብቆ የሚከናወን ስራ አለመሆኑን በመገንዘብ እያንዳንዱ አርሶ አደር በዕለት ተዕለት እንቅስቃሴው የተግባሩ አካል ሊያደርግ እንደሚገባ አሳስበዋል።

በተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ ማብሰሪያ መርኃግብር የተሳተፉ አርሶ አደሮችም የአፈርና ውኃ ጥበቃ ስራ ለም አፈር በጎርፍ ተጠርጎ እንዳይወሰድ በማድረግ ለአፈር ለምነት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተላቸው እንደሚገኝ ጠቁመው ስራው እስኪጠናቀቅ ድረስ በትጋት ለመስራት ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል።

ዘጋቢ: አማኑኤል አጤቦ – ከሆሳዕና ጣቢያችን