ለልማት የሚመደበው ሐብት ለታለመለት ዓላማ እንዲውል የተጠናከረ ክትትልና ቁጥጥር ሊደረግ ይገባል- ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ፀሀይ ወራሳ

ሀዋሳ፡ ጥር 25/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የመንግሥት የልማት ግቦችን ለማሳካት የሚመደበው ሐብት ለታለመለት ዓላማ እንዲውል የተጠናከረ ክትትልና ቁጥጥር ሊደረግ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት  ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ፀሀይ ወራሳ አሳሰቡ።

የክልሉ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት የኦዲት ግኝት ክትትል እና እርምጃ አወሳሰድ ዙሪያ በአርባ ምንጭ ከተማ ምክክር እያካሔደ ነው።

መንግሥት ለልማት የሚበጅተው ሐብት ለታለመለት ዓላማ ስለመዋሉ የአስፈጻሚ አካላት በትኩረት ሐላፊነታቸውን መወጣት እንዳለባቸው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መንግሥት ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ፀሐይ ወራሳ አሳስበዋል።

የኦዲተር መስሪያ ቤቱ የሐብት ብክነት የታየባቸውን ተቋማት የመከታተል እና አስተማሪ የእርምት ርምጃዎችን የማስወሰድ  ሥራ አጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል፡፡

መንግሥት የአገር ኢኮኖሚ እና ማህበራዊ እንቅስቃሴዎችን ማስተዳደር የሚችለው የተጠናከረ የቁጥጥር ስርዓት ስኖር ነው ያሉት ደግሞ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ዋና ኦዲተር አቶ አበባየሁ ኤርሚያስ ናቸው፡፡

የክልሉ ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ገለልተኛ በሆነ መንገድ ግልጽነትን እና ታማኝነት ለማስፈን ከፍ ያለ ሀላፊነትን እየተወጣ ይገኛል ብለዋል።

በቀጣይም ሥራውን በግብረ ሐይል በመምራት የተጠናከረ የኦዲት ስራ ለመስራት ታቅዶ እየተተገበረ ይገኛል ብለዋል።

ዘጋቢ፡ ወ/ገብርኤል ላቀው- ከአርባ ምንጭ ጣቢያችን