የጋሞ ዞን ፖሊስ መምሪያ በህገወጥ መንገድ ሲንቀሳቀስ የነበረን አደንዛዥ እጽ በቁጥጥር ሥር በማዋል እንዲወገድ ማድረጉን አስታወቀ

የጋሞ ዞን ፖሊስ መምሪያ በህገወጥ መንገድ ሲንቀሳቀስ የነበረን አደንዛዥ እጽ በቁጥጥር ሥር በማዋል እንዲወገድ ማድረጉን አስታወቀ

ወጣቱ ይህን አደንዛዥ እጽ በመጠቀም አስፈላጊ ወዳልሆነ ተግባር እየገባ በመሆኑ ህብረተሰቡ ይህን ህገወጥ ተግባር ለመከላከል ከፖሊስ ጎን በመቆም በጋራ እንዲሰራ ጥሪ አቅርቧል።

በህገወጥ መንገድ የሚንቀሳቀሱ አደንዛዥ እጾች እንዲወገዱ መደረጉ በማህበረሰቡ ላይ የሚደርስን አደጋ ከመከላከል አኳያ ድርሻው የጎላ ነው።

በጋሞ ዞን ፖሊስ መምሪያ የህዝብ ግንኙነትና ዲቪዥን ኃላፊ ኮማንደር ረታ ተክሉ እንደተናገሩት ወጣቱ በስብዕና እንዳይታነፅ በህገወጥ መንገድ የሚዘዋወሩት አደንዛዥ ዕፆች አሉታዊ ተፅእኖ እየፈጠሩ መሆኑን አስረድተዋል።

ከዚህ ቀደም በቁጥጥር ሥር ከዋለው በከፍተኛ መጠን ይልቃል ያሉት ኮማንደር ረታ ይህን አይነቱ አደንዛዥ እጽ የሀገር ኢኮኖሚን በከፍተኛ ሁኔታ የሚጎዳ ነው ይላሉ።

ሌላኛው የመምሪያው ኃላፊ ተወካይ ኮማንደር አንተነህ አበበ በበኩላቸው እንዲወገድ የተደረገው ከፍተኛ መጠን ያለው ካናቪስ እና ሺሻ ሲሆን ይህ የእጽ አይነት ደግሞ ወጣቱ ሥራ እንዳይሰራ ከማድረጉም በላይ በሀገር ኢኮኖሚ ላይ ተፅዕኖ ይፈጥራል ብለዋል።

ጎን ለጎንም በህገወጥ መንገድ የሚንቀሳቀሱ ኮንትሮባንዶችና የጦር መሣሪያዎችም ላይ በከፍተኛ ሁኔታ ቁጥጥር ይደረጋል ነው ያሉት።

ይህንን ህገ ወጥ ተግባር የሚፈፅሙ አካላት ለህግ እንዲቀርቡ ይደረጋል ያሉት ኮማንደር አንተነህ፤ ያለ ህብረተሰቡ ተሳትፎ ወንጀልን ፖሊስ ብቻ መቆጣጠር ስለማይችል ህብረተሰቡ ከፖሊስ ጎን እንዲሆኑ ጠይቀዋል።

ዘጋቢ፡ ታምሩ በልሁ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን