የስፖርቱ ዘርፍ የሚያስገኘውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ለማስፋት ሁለም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ፋንታዬ ተናገሩ

አስተዳዳሪው ይህን የተናገሩት የጎፋ ዞን የስፖርት ምክር ቤት 4ኛ መደበኛ ጉባኤውን ባካሄደበት ወቅት ነው።

ጉባኤውን በንግግር የከፈቱት የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪና የምክር ቤቱ ሰብሳቢ አቶ ዳዊት ፋንታዬ ስፖርት በዓለም ላይ ራሱን የቻለ ትልቅ ኢንዱስትሪ መሆኑን ገልጸዋል።

ዘርፉን  ኢኮኖሚ የሚመነጭበት፣ ሠላምና አንድነት የሚሰበክበት እንዲሆን በማድረግ ከዘርፉ የሚገኘውን ጠቀሜታ ለማስፋት ሁለም የድርሻውን ሊያበረክት ይገባል ብለዋል።

ለስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎችን በማዘጋጀትና በማስፋፋት ዘርፉን ውጤታማ ለማድረግ በትኩረት እንደሚሰራ አመላክተዋል።

የጎፋ ዞን ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ ኃላፊና የምክር ቤቱ ፀሐፊ አቶ አወቀ ዓለሙ በበኩላቸው በዞኑ ከ 75 በላይ የስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎች ህጋዊ የይዞታ ማረጋገጫ እንዲኖራቸው የተደረገ ቢሆንም ሌሎች ጉድለቶችን ለቅሞ ማረም እንደሚጠይቅ ጠቁመዋል።

የስፖርቱን  የውድድር መድረኮችን መነሻ በማድረግ በዞኑ  በቋሚና በጊዜያዊ ለ74 ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር ተችሏል ብለዋል።

በጉባኤው የጎፋ ዞን ከፍተኛ አመራሮች፣ የሥራ ኃላፊዎች፣ የወረዳ ዋና አስተዳዳሪዎች፣ የከተማ አስተዳደር ከንቲባዎች እና የስፖርት ፌዴሬሽን አመራሮች ተገኝተዋል።

በጉባኤው የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ግለሰቦች እንዲሁም የወጣቶችና ስፖርት ጽህፈት ቤቶች የዋንጫ እና መዳሊያ ሽልማት ተበርክቷል

ዘጋቢ፡ ድጋፌ ድክሬ – ከሳውላ ቅርጫፍ  ጣቢያችን