“የኢትዮጵያን ሠላም አስጠብቃለሁ፤ ለልጆቼ ምንዳን አስቀራለሁ” በሚል መሪ ቃል የሴቶች ሊግ የንቅናቄ መድረክ በሆሳዕና ከተማ ተካሄደ

በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የሴቶች ሊግ ጽ/ቤት ኃላፊ ወ/ሮ ኤልሳቤጥ ሽመልስ የንቅናቄ መድረኩ ዋና አላማ ሴቶች ስለ ሠላም የሚኖራቸው አበርክቶ ጉልህ መሆኑን በመገንዘብ አበርክቶአቸው የበለጠ እንዲጎላ በማድረግ የኢኮኖሚ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነታቸው ተጠናክሮ የበለፀገች ኢትዮጵያን ብሎም ክልልን ለትውልድ ለማውረስ መላ ሴቶች ሚናቸውን እንዲወጡ ግንዛቤ ለመፍጠርና ወደ ተግባር ለማስገባት መሆኑን ጠቁመዋል።

በክልሉ በየደረጃው በሚፈጠሩ የንቅናቄ መድረኮች ከ600 መቶ ሺህ በላይ ሴቶች እንዲሳተፉ ግብ ጥለው በእንቅስቃሴ ላይ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

ሴቶች በየአካባቢው ያለው አንፃራዊ ሰላም እንዲረጋገጥ የበኩላቸውን ሚና እንዲወጡም ወ/ሮ ኤልሳቤጥ አሳስበዋል።

የሴቶችን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት እና ተሳትፎ የሚያረጋግጡ ተግባራት የሌማት ትሩፋት እና ምግቤን በጓሬዬ በንቃት እንዲተገብሩ፣ የህዳሴ ግድብ የቦንድ ግዢ እና የበጎ አድራጎት ተግባር ላይ ሴቶች በንቃት እንዲሳተፉ፣ የግል ጤናቸውን እንዲጠብቁ ኃላፊዋ ጥሪ አቅርበዋል።

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የፖለቲካና የርዕዮተ ዓለም ዘርፍ ኃላፊ አቶ ይሁን አሰፋ በበኩላቸው ሴቶች ያላቸውን እምቅ አቅም በመጠቀም ስለ ሰላም ብሎም በልዩ ልዩ የልማት ስራዎች ላይ ተሳትፏቸውን በማጠናከር ለሚደረገው የብልፅግና ጉዞ እውን መሆን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳላቸው ጠቅሰዋል።

ሰላምን በማስጠበቅ ረገድ ሴቶች የነበራቸው ሚና ቀላል እንዳልነበር በመግለፅ በቀጣይም በሚደረጉ የልማት ስራዎች እንዲሁም በሰላም እሴት ግንባታ ተሳትፏቸዉን አጠናክረዉ መቀጠል እንደሚገባ አሳስበዋል።

የብልጽግና ፓርቲ ሴቶች ሊግ ሥራ አስፈፃሚ አባል ወ/ሮ አለምነሽ ደመቀ እንደገለፁት መድረኩ የሴቶችን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንደሚቻልና ልማትን ለማሳለጥ ብሎም የሚያጋጥሙ ችግሮችን በወቅቱ ለመፍታት አጋዥ ነው።

ሰላም ለሁሉም ነገሮች መሰረት መሆኑን በመጥቀስ ለሰላም እሴት ግንባታ ሴቶችን በሁሉም ዘርፍ በግንባር ቀደምትነት ማሳተፍ ይገባል ሲሉም አሳስበዋል።

ሴቶች በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊ እንዲሁም የፖለቲካዊ ተሳትፏቸዉን በማጎልበት በጽዳት የተጀመረው የሴቶች የንቅናቄ መድረክ በጤና፣ በትምህርት፣ እንዲሁም በልዩ ልዩ ማህበራዊ ተግባራትን ለማከናወን ይበልጥ ጠቃሚ እንደሆነም ጠቁመዋል።

የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሊሬ ጀማል ሴቶች ሰላምን ለማረጋገጥ ብሎም ለማፅናት ያላቸውን አበርክቶ በማጉላት ለሁለንተናዊ ብልፅግና በጋራ መስራት እንደሚገባ መጠቆማቸውን የክልሉ የመንግስት ኮሙኒኬሽን መረጃ ይጠቁማል።

ሴቶች ሰላም በማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች መሰረት መሆቸውን የጠቆሙት አቶ ሊሬ ሰላምን ለማፅናት የሴቶች ተሳትፎ የጎላ ሚና እንዳለው በመገንዘብ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ አሳስበዋል።