በሴቶችና ህፃናት ዘርፍ ዘላቂ ለውጥ እንዲረጋገጥ ሁሉም አካላት ቀጣይነት ያለው ድጋፍ ማድረግ እንደአለባቸው ተገለጸ

በሴቶችና ህፃናት ዘርፍ ዘላቂ ለውጥ እንዲረጋገጥ ሁሉም አካላት ቀጣይነት ያለው ድጋፍ ማድረግ እንደአለባቸው ተገለጸ

የአሪ ዞን ሴቶችና ህፃናት ጉዳዮች መምሪያ የስድስት ወራት ዕቅድ ክንውን ግምገማና የቀሪ ወራት ዕቅድ ክለሳ መድረክ በተካሄደበት ወቅት ነው ይህ የተገለፀው።

በመምሪያው በኩል የየሥራ ሂደቶች የተከናወኑ ተግባራት ቀርበው ተሳታፊዎች በጥልቀት ተወያይቶባቸዋል።

በሁሉም ዘርፎች ጅምር ለውጦች ቢኖሩም በሴቶችና ህፃናት ዙሪያ ገና በትኩረት መሠራት ያለባቸው በርካታ ጉዳዮች እንደአሉ በመድረኩ ተነስቷል።

የአሪ ዞን ሴቶችና ህፃናት ጉዳዮች መምሪያ ሀላፊ ወ/ሮ ርብቃ አለማየሁ እንደገለፁት መምሪያው ለዘርፉ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ ይገኛል።

በሴቶች ልማት ቡድን አደረጃጀትና ሌሎች አደረጃጀቶች ሴቶች ሁለንተናዊ ለውጥ እንዲያስመዘግቡ በዞኑ ስር ያሉ መዋቅሮች ጠንክረው መሥራት እንዳለባቸው ሀላፊዋ አሳስበዋል።

በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ አጋማሽ የተመዘገቡ ጥንካሬዎች ጎልብተው የተስተዋሉ ድክመቶች ደግሞ ታርመው በዓመቱ ማጠቃለያ ላይ ወጥ የሆነ ውጤት በሁሉም መዋቅር እንዲመዘገብ ቁርጠኝነትን ይጠይቃል ሲልም መመሪያ ኃላፊዋ መልዕክት አስተላልፈዋል።

የአሪ ዞን የመንግስት ዋና ተጠሪና የብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ ጉራልቅ ይዥማልቅ በበኩላቸው በዘርፉ ያለው አመለካከት ከሁሉም ዘንድ ሊጠራ ይገባል ብለዋል።

ሥራዎችን በኢትዮጵያዊነት መንፈስ የጋራ አንድነት በማንፀባረቅ ለተሻለ ለውጥ መስራት ያስፈልጋል ብለዋል አቶ ጉራልቅ።

ሁሉም መዋቅሮች ለዘርፉ ድጋፍ በማድረግ ዘላቂ ውጤት እንዲመዘገብ የድርሻቸውን እንዲወጡም ሀላፊው አሳስበዋል።

የመድረኩ ተሳታፊዎችም በጋራ የተስማሙባቸው ጉዳዮችን ወደ ተግባር ለመቀየር ጠንክረው እንደሚሠሩ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

በመድረኩ በዞኑ ስር ያሉ መዋቅሮች ቀጣይ የሥራ አቅጣጫን የያዘ የጋራ ሰነድ ውል ተፈራርመዋል።

ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ጣቢያችን