የአካል ጉዳተኞች ቀን በጎፋ ዞን ሳውላ ከተማ በልዩ ልዩ ኩነቶች ተከበረ

በበዓሉ ላይ የአርባ ምንጭ አካል ጉዳተኞች ተሀድሶ ማዕከል ለአካል ጉዳተኞች የተለያዩ ድጋፎች አድርጓል፡፡

የአርባ ምንጭ አካል ጉዳተኞች ተሀድሶ ማዕከል አካል ጉዳተኞች የሚደርስባቸውን ስነ ልቦናዊና አካላዊ ጉዳት ከማከም አኳያ በሶስት የስራ ዘርፎች አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝ የማዕከሉ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ ሮማን ሰለሞን ተናግረዋል።

በማዕከሉ ከሚሰጡ አገልግሎቶች መካከል ሰው ሰራሽ የሰውነት አካላቶችን ማቅረብ አንዱ ሲሆን በዚህም ለበርካታ እጅና እግሮቻቸውን በተለያዩ ምክኒያቶች ላጡ አካል ጉዳተኞች አስፈላጊውን አገልግሎት እያበረከተ እንደሚገኝ የዘርፉ ባለሙያ አቶ ወንዱ አለማየሁ ገልጸዋል።

በዓሉን ምክኒያት በማድረግ ወዲያውኑ ሊታከሙ የሚችሉትን የማከም እና ሰው ሰራሽ የሰውነት አካል፣የክራንችና ዊልቸር ድጋፍ አድርጓል፡፡

በዕለቱ በአካል ጉዳተኞች የተመረቱ ልዩ ልዩ የቆዳ ውጤቶች ለሽያጭ ቀርበዋል፡፡ አምራቾቹ የሰው እጅ ከማየት ሰርተው መተዳደር እንደሚችሉ ያሳየ ተግባር እንደሆነም ተገልጿል።

የጎፋ ዞን ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ መምሪያ ኃላፊ አቶ ተመስገን ጌታቸው ከአርባምንጭ የአካል ጉዳተኞች ተሀድሶ ማዕከል ጋር በመነጋገር የዞኑን አካል ጉዳተኞች ተጠቃሚ ለማድረግ በጋራ እየተሰራ መቆየቱን ተናግረዋል፡፡

ከማህበሩ በርካታ ልምዶች የሚወሰድ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

ዘጋቢ: አወል ከድር – ከሳውላ ጣቢያችን