የዞኑን ሰላም ለማስጠበቅና የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥ በቁርጠኝነት መንቀሳቀስ እንደሚያስፈልግ የጋሞ ዞን ፖሊስ መምሪያ ገለፀ

መምሪያው በ2ዐ16 በጀት ዓመት 6 ወራት አፈፃፀም ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር የምክክር መድረክ በማካሄድ ላይ ይገኛል።

በመክፈቻ መድረኩ የዞኑ ፖሊስ መምሪያ አዛዥ ዋና እንስፔክተር ደበበ ኦንቶ፤ ፖሊስ የዞኑን ሠላም ለማስጠበቅ እና የህግ የበላይነት እንዲከበር የተሰጠውን ተልዕኮ በብቃት ለመወጣት እያደረገ ያለውን አኩሪ አድንቀዋል።

በቀጣይም ህብረተሰቡን ከጎኑ በማሰለፍ ለዘላቂ ሠላም እና የህግ የበላይነት ማስከበር በቁርጠኝነት መንቀሳቀስ ያስፈልጋል ብለዋል።

ህብረተሰቡ ወንጀል እንዲከላከል ስለ ወንጀል አስከፊነት ትምህርቶችን ከመስጠት ባሻገር በህገወጥ የኮንትሮባንድ ንግድ ላይ የተሰማሩ ግለሰቦችን በመከታተል ለህግ የማቅረቡ ሂደት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አሳስበዋል የፖሊስ አዛዡ።

በስድስት ወራት ውስጥ በህገወጥ መንገድ ሲዘዋወር የነበረ 18 ሽጉጥ፣ 54 የሽጉጥ ጥይት፣ 6 ክላሽ ጠመንጃ፣ 325 ኋላቀር የጦር መሳሪያ፣ 8 ጥይት፣ 60 ኤፍ ዋን ቦምብ ከ3 ተጠርጣሪዎች ጋር በቁጥጥር ስር ማዋል መቻሉን ተናግረዋል።

በመድረኩ ከሁሉም ወረዳዎች እና ከተማ አስተዳደሮች የተወጣጡ የፖሊስ አዛዦች እና የማህበረሰብ አቀፍ ወንጀል መከላከል አስተባባሪዎች የተሳተፉ ሲሆን የ2016 በጀት ዓመት 6 ወራት አፈፃፀም ቀርቦ ውይይት ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ዘጋቢ፡ ንጋቷ ይስሀቅ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን