የኢትዮጵያን ስብራቶች በመጠገን ሁለንተናዊ ልማትና እድገት የማረጋገጥ ጉዳይ በለውጡ ሂደት ዋነኛ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ ነው

የኢትዮጵያን የቆዩ ስብራቶች በመጠገን ሁለንተናዊ ልማትና እድገት የማረጋገጥ ጉዳይ በለውጡ ሂደት ዋነኛ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማህበራዊ ዘርፍ አማካሪ ሚኒስትር ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) “ፀሐይ” አውሮፕላንን ከጣልያን መንግሥት በይፋ በተረከቡበት ወቅት ቀኑ ለኢትዮጵያውያን ታላቅ የኩራት ቀን መሆኑን ተናግረዋል።

በ1920 ዘመናዊ ጥበብ ሲጀመር ቅድሚያ ከተሰጣቸው ዘርፎች መካከል አንዱ የአቪየሽን ዘርፍን ማስፋፋት ነበር፡፡

ኢትዮጵያም በወቅቱ አውሮፕላን በመግዛት የጀመረችውን ጉዞ “ፀሐይ” የተባለችውን አውሮፕላን በመስራት ወደ አዲስ ምዕራፍ መሸጋገሯን የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማህበራዊ ዘርፍ አማካሪ ሚኒስትር ዲያቆን ዳንኤል ክብረት አስታውሰዋል፡፡

“ፀሐይ” በ1928 ዓ.ም በጀርመናዊው ኢንጂነር እና የንጉሱ ፓይለት ሄር ሉድዊግ ዌበር ብሎም በወቅቱ በነበሩ ኢትዮጵያዊያን ባለሞያዎች ትብብር በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የተሰራች አውሮፕላን ናት።

አውሮፕላኗ ላለፉት 88 ዓመታት በጣሊያን የቆየች ሲሆን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ባደረጉት ያላሰለሰ ጥረት ወደ ኢትዮጵያ መመለሷን ጠቅሰዋል፡፡

ለውጡን ተከትሎ የኢትዮጵያን ስብራቶች ለመጠገን ዘርፈ ብዙ ጥረቶች እየተደረጉ መሆኑን ጠቅሰው የአውሮፕላኗ መመለስም የዚሁ ጥረት ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል።

በለውጡ ሂደት እየተከናወኑ ካሉ ተግባራት መካከል የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ስብራቶች በመጠገን የኢትዮጵያን እድገትና ብልጽግና ማረጋገጥ ነው ብለዋል።

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ጥረት “ፀሐይ” አውሮፕላን ከጣሊያን ወደ ኢትዮጵያ መመለስ መቻሏ ኢትዮጵያዊያን ራሳቸውን ለመቻል በነበራቸው ጥረት የደረሰውን ስብራት በመጠገን ጉዞውን ማስቀጠል ነው ብለዋል።

የአውሮፕላኗ መመለስ ትውልዱ ያለፈውን አውቆ ለሚመጣው ጊዜ ተነሳሽነት እንዲኖረው ለማድረግ የሚያስችል መሆኑንም ተናግረዋል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)፤ ለአንድ ዓመት ያክል ከጣልያን ጠቅላይ ሚኒስትር ጂኦርጂያ ሜሎኔ ጋር አውሮፕላኑ መመለስ በሚችልበት ሁኔታ ላይ ሰፊ ንግግር ሲያደርጉ መቆየታቸው ይታወቃል።