ለኢንቨስትመንት የሚሆን የመሬት ዝግጅት መደረጉን የኬሌ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ

ሀዋሳ፡ ጥር 22/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በኮሬ ዞን ኬሌ ከተማ አስተዳደር ለኢንቨስትመንት የሚሆን መሬት እያዘጋጀ መሆኑን አስታውቋል፡፡

በኮሬ ዞን የኬሌ ከተማ አስተዳደር ዋና ከንቲባ አቶ ዮሐንስ ሐይሉ እንደተናገሩት፣ ከተማዋ በ2012 ዓ.ም የከተማ አስተዳደር ከሆነችበት ጊዜ አንስቶ ሰፊ የመሰረተ ልማትና የውበት ሥራዎች እየተከናወኑ ናቸው።

የጌጠኛ ድንጋይ ንጣፍ፣ የጎርፍ መቀልበሻዎች፣ የመንገድ ከፈታዎችና ሌሎች የልማት ሥራዎች ላይ በጀት ተይዞ በ”ማቺንግ ፈንድም” ድጋፍ ስለመሠራቱ ከንቲባው ገልጸዋል።

ከተማዋን አርንጓዴ ማልበስ የሚያስችሉ ሥራዎች እንደተሠሩ እና ከዚህ በፊት ተሰርቶ በማይታወቀው የመሬት ዝግጅት ዘርፍም በተከናወነው ተግባር በሊዝ ማስተላለፋቸውን ተናግረዋል።

በከተማው የልማት እንቅስቃሴ ላይ ሕዝቡ እያሳየ ያለው በጎ ምላሽ፣ መልካም እንደሆነም አመላክተዋል።

ዘንድሮ በሆቴልና መዝናኛዎች፣ በትምህርት ዘርፍ በኮሌጆች እና በነዳጅ ማደያ ኢንቨስት ማድግየሚፈልጉ ባለሀብቶችን ለመጋበዝ ዝግጅት መደረጉን ገልጸዋል።

እስካሁን 4 ሺህ 6 መቶ ካሬ ሜትር በላይ መሬት ለኢንቨስትመንት ተዘጋጅቷል፤ ቅድመ ዝግጅቱ 90 በመቶ ተጠናቋል ብለዋል።

የሚሠሩ የልማት ሥራዎች እንዳይስተጓጎሉ አሁን ላይ የመንገድ ከፈታ ሥራን ከተማ አስተዳደሩ መጀመሩን ገልጸዋል።

ከዚህ በፊት ነባር ቦታ ወስደው ያላለሙ አካላትም የሕዝቡን የልማት ጥማት ለመመለስ እንዲያለሙም ከተማ አስተዳደሩ አሳስቧል።

ዘጋቢ ፡ እስራኤል ቅጣው – ከይ/ጨፌ ጣቢያችን