የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልላዊ መንግስት እና የካፋ ማህበረሰብ ቴሌቪዥን በጋራ በሚሰሯቸው ጉዳዮች የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረሙ

የመግባቢያ ስምምነቱን የክልሉ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ከካፋ ማህበረሰብ ቴሌቪዥን ጋር ተፈራርመዋል።

በስምምነቱ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ ስምምነቱ በክልሉ የሚከናወኑ የፖለቲካ፣ የማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ተግባራትን ለህብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ ያግዛል ብለዋል።

የካፋ ማህበረሰብ ቴሌቪዥን በክልሉ መኖሩ አንድ ለውጥ ነው ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ ዘመኑን የዋጀ አገልግሎት ለመስጠት ተደራሽነቱን ማጠናከር ይኖርበታል ብለዋል።

ክልላዊ የሚዲያ ተቋም በክልሉ እስከሚደራጅ የክልሉ መንግስት ሚዲያውን ማብቃትና ማጎልበት እንደሚገባም ተናግረዋል።

የተፈጸመው የጋራ መግባቢያ ሰነድ ክልላዊ አንድነትንና አካባቢያዊ ትብብርን የሚያጠናክር የሠላምና የልማት መስክ ነውም ብለዋል ርዕሰ መስተዳድሩ።

የክልሉ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ የሺዋስ ዓለሙ አሁን ላይ ያሉት የመረጃ ልውውጥ ስራዎች በማህበራዊ ሚዲያ ላይ የተንጠለጠሉ መሆናቸውን ተናግረዋል።

ከካፋ የማህበረሰብ ቴሌቪዥን ጋር የተደረገው ሁለትዮሽ ስምምነትም የአየር ሰዓት በመከራየት ለመስራት የታሰበ ነዉ ብለዋል።

የካፋ ማህበረሰብ ቴሌቪዥን ዋና ስራአስኪያጅ አቶ አስራት ሀይሌ ስምምነቱ ተደጋግፈን በመስራት ሚዲያው እንዲያድግ የሚያግዝ ነው ብለዋል።

በተደረገው ስምምነትም ክልላዊ የፖለቲካ፣ የማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ስራዎችን አጠናክረን ለመስራት የሚያስችል መሆኑን አቶ አስራት መናገራቸውን ከክልሉ የመንግስት ኮሙኒኬሽን የተገኘ መረጃ ያመለክታል።