በዘንድሮ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ከ420 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት ይለማል – የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ

ሀዋሳ፡ ጥር 22/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በዘንድሮ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ከ420 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት እንደሚለማ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ አስታወቀ።

በልማት ስራው ከ2 ሚሊየን 600 ሺህ በላይ ህዝብ እንደሚሳተፍም ተጠቁሟል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ በጋሞ ዞን አርባምንጭ ዙሪያ ወረዳ ጋንታ መይጨ ቀበሌ “በተደራጀ የህዝብ ንቅናቄ የሚፈፀም የተቀናጀ ተፋስ ልማት ለሁለንተናዊ ብልፅግና” በሚል መሪ ቃል የክልሉ ቢሮ ኃላፊን ጨምሮ የቢሮ ማኔጅመንት አባላትና የተጠሪ ተቋማት የስራ ኃላፊዎች በተገኘበት በይፋ ተጀምሯል።

በተፋሰስ ልማት ስራ ባለፉት አመታት የተቀመሩ ምርጥ ተሞክሮዎችን በማስፋት ንዑስ ተፋሰሶችን ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ነፃ አድርጎ መልማት እንዳለበት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ኃ/ማሪያም ተስፋዬ አሳስበዋል።

ለተከታታይ 30 ቀናት በክልሉ ሁሉም አካባቢዎች የሚተገበረው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ለተራራ ልማትና ለጠረጴዛማ እርከን ስራ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሰራም ተጠቁሟል።

ዘጋቢ፡ ሰናይት ካሳ