በደቡብ ኦሞ ዞን ሣላማጎ ወረዳ የ2016 ዓ.ም የተፋሰስ ልማትና የበልግ ሥራዎች ንቅናቄ በሃና ከተማ ተካሄዷል።
መድረኩን በንግግር የከፈቱት የወረዳው ግብርና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ካድሱ ካሻሌ እንደገለፁት፤ የተፋሰስ ልማት የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል፤ ብዝሃ ሀብቶችን ለማስጠበቅ ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር እንደሚረዳ ገልፀው በእስከዛሬው ሂደትም የአርሶ አርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ለወጥ ያመጣ እንደሆነ አመላክተዋል።
አክለውም የሥነ-አካላዊ እና ሥነ-ህይወታዊ ሥራዎችን በማጠናከር በተያያዘም የበልግን ሥራ በውጤታማነት ለመፈፀም ሁሉም ባለድርሻ አካላት እንዲረባረቡም አሳስበዋል።
የወረዳው ግብርና ጽ/ቤት የተፋሰስ ልማት ጥናትና ዲዛይን ባለሙያ አቶ ያንተአለ ላቀው በዘንድሮ 2016 ዓ.ም የተፋሰስ ልማት ሥራ አጠቃላይ 32ሺህ አባወራ፣ እማወራ እና ወጣቶችን በማሳተፍ 24ሺህ ሄክታር መሬት ለማልማት ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን ገልፀዋል።
በመድረኩም መነሻ ሰነድ ቀርቦ ሰፊ ውይይት ተካሄዶበታል።
ከተሣታፊዎች መካከል አቶ ሉች ናበጋስ ፤ ጌታሁን ማሞ እና ሌሎችም በሰጡት አሰተያየት ከዚህም ቀደም በነበሩ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች ምርታማነታቸው እንደጨመረ ገልፀው በዘንድሮውም በተሻለ መንገድ ለመስራት በንቅናቄ ተሳትፈው እንደሚያሳትፉ ተናግረዋል።
ዘጋቢ፡ ደፋሩ ስፍታዬ – ከጂንካ ጣቢያችን
More Stories
ቆሻሻን በአግባቡ በማስወገድ ከተማዋ ፅዱና ውብ እንድትሆን የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ነው – የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት
በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች በቋሚነት የሚደገፉበት ስራ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የቡርጂ ዞን አስተዳደር አስታወቀ
“አንድ ሰው ወደዚህች ምድር ሲመጣ እንዲሰራ የተፈቀደለትና የሚጠበቅበት ነገር አለ” – ታደሰ ገብሬ /ጃክሰን/