ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በጉራጌ ዞን አጀንዳ የሚሰጡ የማህበረሰብ ክፍል ተወካዮች መረጣ መድረክ በነገው እለት በወልቂጤ ከተማ ማካሄድ እንደሚያካሂድ አስታወቀ

ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በጉራጌ ዞን አጀንዳ የሚሰጡ የማህበረሰብ ክፍል ተወካዮች መረጣ መድረክ በነገው እለት በወልቂጤ ከተማ ማካሄድ እንደሚያካሂድ አስታወቀ

ኮሚሽኑ መድረኩን በማስመልከት መግለጫ ሰጥቷል።

የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ሙሉጌታ አጎ በሰጡት መግለጫ ኮሚሽኑ በቀጣይ ለሚያካሄደው ሀገራዊ ምክክር ውጤታማነት አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት ማድረጉን ገልፀዋል።

በዚህም እስካሁን ባለው ሂደት በሀገሪቱ በሚገኙ በ6 ክልሎች እና በ2 ከተማ አስተዳደሮች የውይይት መድረክ ማካሄዱን አመላክተዋል።

በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በጉራጌ ዞን አጀንዳ የሚሰጡ የማህበረሰብ ክፍል ተወካዮች መረጣ ከነገ ጥር 21-23/2016 ዓ.ም ድረስ ለ3 ተከታታይ ቀናት በወልቂጤ ከተማ እንደሚያካሄድም ነው የገለፁት::

በተወካዮች መረጣው ላይም ከዞኑ ከሚገኙ ወረዳዎችና ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች የሚሳተፉ ሲሆን የሚወከሉትም ከሴቶች፣ ወጣቶች፣ የንግዱ ማህበረሰብ፣ መምህራን፣ አርሶ አደሮች፣ የማህበረሰብ መሪዎች፣ እድሮችና ከመንግስት ሰራተኞችና ከሌሎችም የተውጣጡ ሰለመሆናቸው ነው ኮሚሽነሩ በመግለጫቸው ያመላከቱት።

የመረጣው ሂደት አካታች፣ ግልፅ፣ አሳታፊና ተአማኒነትን ያገናዘበ እንዲሆን ይደረጋል ያሉት ኮሚሽነር ሙሉጌታ በሂደቱም ከዞኑ ከሚወከሉ ከእያንዳንዱ የማህበረሰብ ክፍል ሁለት ሁለት ተወካዮችና አንዳንድ ተጠባባቂዎች እንደሚመረጡም ገልፀዋል።

ከነገ ጀምሮ ለሶስት ተከታታይ ቀናት የሚካሄደውን ከህብረተሰቡ የሚቀርቡትን አጀንዳዎች በማሰባሰብ ለኮሚሽኑ የሚያቀርቡ ተወካዮች መረጣ በተሳካ ሁኔታ እንዲጠናቀቅ ባለድርሻ አካላት የድርሻቸውን እንዲወጡም ኮሚሽኑ ጥሪውን አቅርቧል።

ዘጋቢ፡ ሚፍታ ጀማል- ከወልቂጤ ጣቢያችን