የሴቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ  ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ

የሴቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ  ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ

ሀዋሳ፡ ጥር 17/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሴቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ  ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን የጋሞ ዞን ሴቶችና ህፃናት መምሪያ አስታወቀ።

መምሪያው የሴት አርሶ አደሮችን የልማት እንቅስቃሴ በአርባምንጭ ዙሪያ ወረዳ ተገኝቶ የመስክ ጉብኝት አድርጓል።

የጋሞ ዞን ሴቶችና ህፃናት መምሪያ ኃላፊ ወ/ሪት  ሠላመዊት ቦዳ የሴቶችን ማህበራዊ ፣  ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ተጠቃሚነት ይበልጥ  ለማረጋገጥ   የልምድ ልውውጥ  እንዲያደርጉ  መደረጉን ተናግረዋል።

አክለውም በተለይም ሞዴል ሴት አርሶ አደሮችን ተሞክሮ ለማስፋት  በቅንጅት እየተሰራ እንደሚገኝ  የሚናገሩት ኃላፊዋ ሴቶች   ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እንዲያረጋግጡ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

ሴቶች በሌማት ትሩፋት ላይም ተሰማርተው የኑሮ ጫናን መቋቋም እንዲችሉ አቅም የማጎልበት ሥራም ተጠናክሮ መቀጠሉን አስረድተዋል።

ጠንካራ  ሴት አርሶ አደሮችን ራዕይ የማሰቀጠል  ተግባራትን አስተሳስሮ መሄድ ይጠበቅብናል ያሉት ኃላፊዋ ሁሉም አካል  ተሞክሮውን ወደ ተግባር እንዲቀይር ጠይቀዋል ።

 በአርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ የኦቾሎ ላንቴ   ቀበሌ ካሉት ሞደል ሴት አርሶ አደሮችና መካከል ወ/ሮ አይናአበባ አስፋ አንዷ ናቸው።

ቲማቲም  እና ሌሎች የጓሮ አትክልትን በማልማት በዘርፉ ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውን ተናግረው በ10 ሚሊዮን  ብር  ወጪ በማድረግ የምርጥ የዘር ድርጅት ለመክፈት እንቅስቃሴ ላይ መሆናቸውን አውስተዋል።

በመስክ ጉብኝቱ በዞኑ የሚገኙ ከወረዳና ከተማ አስተዳዳሪዎች የተወጣጡ ሴት አመራሮች የተገኙ ሲሆን ከመስክ ምልከታው ብዙ ልምድ እንደቀሰሙ ጠቁመዋል ።

በመጨረሻም ለሞዴል አርሶ አደር አይናበባ በዞኑ ሴቶች መምሪያ በኩል የእውቅና ሽልማት ተበርክቶላቸዋል ።

ዘጋቢ ፡ አበበ ዳባ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን