የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ

ሀዋሳ፡ ጥር 10/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ የከተራና የጥምቀት በዓል በክልላችን ሁሉም አካባቢዎች በድምቀት ከሚከበሩ ሀይማኖታዊ በዓላት አንዱ ነው ሲሉ ገልጸዋል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የአደባባይ በዓላት ከሆኑት አንዱ ጥር 11 ቀን ላይ የሚውለው የጥምቀት በዓል ነው፡፡

ርዕሰ መስተዳድሩ በዓሉን ምዕመናንና ካህናት በመንፈሳዊ ዝማሬዎች ታቦታቱን አጅበው ወደ ጥምቀተ ባህር በመውረድ በድምቀት የሚያከብሩት በዓል ነው ብለዋል።

የክልላችን የክርስትና ዕምነት ተከታዮች በዓሉን ሲያከብሩ በፍጹም የዕምነቱ አስተምህሮ ሰላምን በመሰበክ ሊሆን ይገባል ብለዋል።

የሀይማኖት አባቶች እንደወትሮው ሁሉ አስተምህሯቸው ሰላምን የሚሰብክ የሌሎች ዕምነት ተከታዮችን በማክበርና በመቀራረብ በአብሮነት መንፈስ በዓሉን ማክበር ይኖርባቸዋል ሲሉም ገልጸዋል።

ርዕሰ መስተዳድሩ የከተራና የጥምቀት በዓል በዓለም ከማይዳሰሱ ቅርሶች አካል አንዱ በመሆኑ እንደሌሎቹ በዓላት ሁሉ ያለ ምንም የጸጥታ ችግር እንዲከናወን ምዕመናን፣ ወጣቶች ከጸጥታው አካላት ጋር በመሆን የድርሻቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።

መላው የሀገራችንና የክልላችን የክርስትና እምነት ተከታዮች በዓሉ የኢትዮጵያውያን በዓል በመሆኑ በችግር ውስጥ ሆነው የሚያከብሩትን በመደገፍ፣ ላጡት በመለገስ፣ በፍቅርና በአብሮነት ሊያከብሩ ይገባልም ማለታቸውን ከክልሉ የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን የተገኘ መረጃ ያመላክታል።

በዓሉ የሰላም፣ የፍቅር፣ የአብሮነትና የመተሳሰብ እንዲሆንላች እመኛለሁ ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።