የዲላ ከተማ ማዘጋጃ ቤት የመሠረተ ልማት ችግሮችን ለመፍታት ወደ ተግባር መግባቱን ገለጸ

የዲላ ከተማ ማዘጋጃ ቤት የመሠረተ ልማት ችግሮችን ለመፍታት ወደ ተግባር መግባቱን ገለጸ

ሀዋሳ፡ መስከረም 24/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ህብረተሰቡን አስተባብሮ የመሠረተ ልማት ችግሮችን ለመፍታት ወደ ተግባር መግባቱን የዲላ ከተማ ማዘጋጃ ቤት ገልጿል፡፡

የዲላ ከተማ ነዋሪዎች አቶ ንጉሴ ጤኮ፣ ዳኛቸው ሀብተማሪያም እና ሌሎችም ለልማት ካላቸው ፍላጎት የተነሳ አዲስ ለመንገድ ከፈታ ሥራ መተዳደሪያቸው የሆኑ ሰብሎችንና ፍራፍሬዎችን ያለምንም ክፍያ ከቦታው እያነሱ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡

አሁን ያሉበት አካባቢ ከአሥር ዓመት በፊት በከተማ ሥር የተካለለ ቢሆንም መንገድ ባለመኖሩ ምክንያት ለመብራት፣ ውሃ እና ሌሎች መሠረተ ልማት ችግሮች ተዳርገው መቆየታቸውን ገልጸዋል፡፡

ህብረተሰቡ መተዳደሪያው የሆነውን የቡና፣ ሙዝ፣ ማንጎ፣ አቡካዶና የተለያዩ ሰብሎችን በፈቃዳቸው ያለክፍያ እንዲያነሳ ከህብረተሰቡ ጋር ተወያይቶ በመግባባት አራት አዳዲስ መንገዶችን ማስከፈታቸውን የሆሰ ዴላ ቀጠና አስተዳዳሪ አቶ ግርማ ምህረቱ ተናግረዋል።

የዲላ ከተማ ማዘጋጃ ቤት ሥራ አስኪያጅ አቶ ምንተስኖት ከበደ ማህበረሰቡ ለመሠረተ ልማት ሥራ ያለውን ፍላጎት አድንቀው ለቀና ትብብሩም አመስግነዋል ።

በበጀት ዓመቱ በህብረተሰብ ተሳትፎ 18 ኪሎ ሜትር እና በማዘጋጃ ቤት 18 ኪሎ ሜትር በድምሩ 36 ኪሎ ሜትር አዲስ መንገድ ለመገንባትመታቀዱን አስታውቀዋል፡፡ እስከአሁን በህብረተሰቡ ከ4 ኪሎ ሜትር በላይ መሰራቱን ያነሱት ሥራ አስኪያጁ፥ የጎላ የመንገድ ችግር ካለባቸው ቀበሌያት ሀሮ ወላቡና ሀሮሬሳ ላይ ትኩረት እንደሚደረግ አስረድተዋል ።

በከተማው መንገድ በሌለባቸው አካባቢዎች ህብረተሰቡ መሠረት ልማቶችን ጨምሮ ሌሎች አገልግሎቶችን እያገኘ ባለመሆናቸው በቀጣይ አካባቢዎቹ የመንገድ፣ ዲቺ፣ መብራት፣ ውሃ፣ ካርታና ሌሎች አገልግሎቶችን ያገኛሉ ብለዋል።

ሌሎች ቀበሌያትም ይህን ልምድ በመውሰድ ከተማውን ለማልማትና ለማሳደግ ከመንግሥት ጎን እንዲቆሙ ጥሪ አቅርበዋል።

ዘጋቢ፡ ተሰፋዬ ጎበና- ከፍስሃ ገነት ጣቢያችን