በሳጃ ከተማ በ5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው የሚሊኒየም ቁጥር ሁለት የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ተጠናቆ ለአገልግልት ክፍት ሆነ

የትምህርት ቤቱ ግንባታም የ2015 የበጎ ፈቃድ አገልግሎት “በጎነት ለኢትዮጵያ ከፍታ” በሚል መርህ በተካሄደበት ወቅት በኢትዮ ኢንጅነሪንግ በጎ አድራጎት ግሩፕና በቀድሞ የደቡብ ክልል ትምህርት ቢሮ በ5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ብር ወጪ የግንባታና የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ መመረቁ ተገልጿል::

ግንባታዉ ተጠናቆ በዛሬው ዕለት ለአገልግሎት ክፍት የሆነዉ የሚሊኒየም ቁጥር ሁለት የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ሁለት ብሎክ ያለዉ ሲሆን ስምንት መማሪያ ክፍሎችንና የመምህራን ማረፊያዎችን እንዲሁም መፀዳጃ ቤት ያካተተ ነዉ ተብሏል::

ግንባታዉም በአጭር ጊዜና በጥራት ተገንብቶ መጠናቀቁን በምረቃው ወቅት ተገልጿል::

የትምህርት ቤቱ መመረቅ ቀደም ሲል ረጅም መንገድ በመጓዝ ሲማሩ የነበሩ ተማሪዎችን ችግር የቀረፈ መሆኑን ተማሪዎችና ወላጆች ተናግረዋል::

ትምህርት ቤቱ በዘንድሮ የትምህርት ዘመን ከ 6 መቶ በላይ ተማሪዎችን ተቀብሎ በሁለት ፈረቃ የመማሪ ማስተማር ስራ መጀመራቸዉን በዕለቱ ተገልጿል::

በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የዉጭ ጉዳይ ሚንስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አረጋ፣ የብልጽግና ፓርቲ ስራ አስፈጻሚና የአዲስ አበባ ከተማ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ሞገስ ባልቻ፣ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ፋጤ ስርሞሎ፣ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የመንግስት ረዳት ተጠሪ አቶ ይሁን አሰፋን ጨምሮ የተለያዩ የፌዴራልና የክልል የመንግስት ስራ ኃላፊዎችና ምሁራን እንዲሁም የአካባቢዉ ወላጆችና ተማሪዎች ተገኝተዋል፡፡

ዘጋቢ፡ ተዘራ በቀለ – ከወልቂጤ ጣቢያችን