በጌዴኦ ዞን ዲላ ከተማ አስተዳደር ወጣቶችና ሰፖርት ጽ/ቤት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ማጠቃለያ መድረክ ተካሄደ

በጌዴኦ ዞን ዲላ ከተማ አስተዳደር ወጣቶችና ሰፖርት ጽ/ቤት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ማጠቃለያ መድረክ ተካሄደ

በሀገር አቀፍ ደረጃ “በጎነት ለኢትዮጵያ ከፍታ” በሚል መሪ ቃል ሲካሄድ የነበረው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ሥራ በዛሬው ዕለት በዲላ ከተማ ጌዴኦ ባህል አዳራሽ የማጠቃለያ ኘሮግራም በመካሄድ ላይ ነው።

የማጠቃለያ መርሃ ግብሩን ያስጀመሩት የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዶ/ር ዝናቡ ወልዴ የጌዴኦ መልክአ ምድር በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ ሳይንስና ባህል ድርጅት በመመዝገቡ እንኳን ደስ አላችሁ ብለው ባለፉት ሁለት ወራት ጉልበት ሳይሰስቱ የማህበረሰቡ ችግር የኔ ችግር ነው ብለው ማህበራዊ ኃላፊነታቸውን የተወጡት ወጣቶችን አበረታተዋል።

በዞኑ በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ወጣቶች አንድ ሺህ አራት መቶ ቤቶች መጠገናቸውንና መገንባታቸውን የተናገሩት ዋና አስተዳዳሪው በቀጣይም ከተባብርን በርካታ ችግሮች ውስጥ ያሉ ማህበረሰብ ክፍሎችን በመድረስ ችግራቸውን ማቃለል እንችላለን ብለዋል።

የዲላ ከተማ ከንቲባ አቶ ዳንኤል ሽፈራው “በጎነት ለኢትዮጵያ ከፍታ” በሚል ሲካሄድ የነበረው የ2015 ዓ.ም የወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት ማጠቃለያ ኘሮግራም እና የ2016 በጀት የበጋ አገልግሎት መክፈቻ ሥነ ሥርዓት በማካሄድ እንገኛለን ሲሉ ተናግረዋል።

የአቅመ ደካማ ቤቶችን መገንባትና መጠገን፣ የትራፊክ አደጋን መከላከል፣ የከተማ ጽዳትና ሌሎችም አሥራ አምስት ተግባራት ላይ ተሳትፈው የህዝቡን ችግር ፈቺ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ማህበራዊ ኃላፊነት ሰለተወጡ አመስግነዋል።

የዲላ ከተማ አስተዳደር ወጣቶችና ስፖርት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ መላኩ አየለ በከተማው በርካታ ወጣቶች ተሳትፈው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸው ተግባራትን ማከናወናቸውን ተናግረዋል።

በዚሁ ተግባር ከሃያ አንድ ሺህ በላይ ወጣቶች ተሳትፈው በሰጡት አገልግሎት ከሠማኒያ ሰባት ሺህ ሰባት መቶ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ በማድረግ ከመንግስት ካዝና ይወጣ የነበረውን አሥራ ሰባት ሚልየን ሰባት መቶ ስልሳ አንድ ብር ማዳን ተችሏል ብለዋል።

ዘጋቢ፡ ተስፋዬ ጎበና – ከፍስሃገነት ጣቢያችን