የመስቀል በዓል በዩኒስኮ እንደተመዘገበ ሁሉ በዳዉሮ የንጉስ ሃላላ የድንጋይ ኬላም ዕውቅና አግኝቶ እንዲመዘገብ ለማስቻል በተቀናጀ ጥረት ሊሠራ እንደሚገባ ተገለፀ
ሀዋሳ፡ መስከረም 17/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የመስቀል በዓል በዩኒስኮ እንደተመዘገበ ሁሉ በዳዉሮ የንጉስ ሃላላ የድንጋይ ኬላም ዕውቅና አግኝቶ እንዲመዘገብ ለማስቻል በተቀናጀ ጥረት ሊሠራ እንደሚገባ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የዳዉሮ እና ኮንታ አህጉረስብከት ሊቀጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል አቡነ ጢሞቴዎስ ተናገሩ።
የንጉስ ሃላላ የድንጋይ ካብ እንዲመዘገብ እና ሌሎች የሕዝብ የቱሪዝም ሃብትና ቅርስ የሆኑት ተጠብቀው እንዲኖሩ ቤተክርስቲያኗ ከመንግሥት ጋር በጋራ ጉዳዮች ተባብራ እንደምትሰራም ነው የገለጹት።
በዕለቱ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ተወካይና የፋይናንስ እና ኢኮኖሚ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ዳዊት ገበየሁ በበኩላቸው መስቀል የድልና የፍቅር መገለጫ በመሆኑ ድህነትን ለማሸነፍ የሚደረገውን ጥረት ምዕመናን በተሠማሩት የሥራ ዘርፍ ውጤታማ ተግባር እያከናወኑ፣ የተቸገሩትን በፍቅር ተገቢ እንክብካቤ በመስጠት ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን መወጣት እንዳለባቸውም ገልጸዋል።
በዳዉሮ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ታሪክ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ሊቀጳጳስ በመስቀል አደባባይ ተገኝተው ያከበሩበት በዓል ለከተማው ልዩ አጋጣሚ መሆኑን የተርጫ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ዳዊት ወንድሙ ገልጸዋል።
ክርስቲያን ወገኖች በዓሉን ሲያከብሩ አንድነትን በማጠናከር፣ ለአካባቢያቸው ሰላም ዘብ መቆም እንዳለባቸውም ተገልጿል።
በቦታው ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የተርጫ ከተማ ከንቲባ በህገ መንግሥቱ በተቀመጠው የአሠራር ሥርዓት በመታገዝ ለሕዝቡ ተጠቃሚነት ከሃይማኖት ተቋማት ጋር በአስተዳደራዊ፣ በማኅበራዊ፣ ኢኮኖያሚያዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች በጋራ ለመሥራት ቁርጠኛ መሆናቸውንም ገልጸዋል።
ዘጋቢ፡ መሣይ መሠለ – ከዋካ ጣቢያችን

More Stories
በተሰማሩበት የስራ ዘርፍ ተገቢውን ትኩረት መስጠትና ተግቶ በመስራት ከድህነት መውጣት ይገባል – ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
ኢትዮጵያን ለዘመናት ከቆየችበት ቁስል ለማላቀቅ ባለፉት የለውጥ አመታት በርካታ ፖለቲካዊ ተግባራት ማከናወኑን መቻሉ ተገለጸ
ችግር ፈቺ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ስራዎችን በመስራታቸው ዘርፈ ብዙ ጠቄሜታ ማግኘታቸውን የአርባምንጭ ፖሊ ቴክኒክና ሳታላይት ኮሌጅ ተማሪዎችና መምህራን ገለፁ