ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ ለደመራ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አሰተላለፉ
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ ባስተላለፉት መልዕክት በበዓሉ ወቅት ተቸገሩትን በመርዳት ልናከብር ይገባል ብለዋል።
ለዘመናት ተቀብሮ የኖረው የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ከተጫነው ተራራ ከተደበቀበት ስውር ስፍራ ይወጣ ዘንድ በደመራ ሰማያዊ ምልክት የታየበትን ቀን ለምናከብርበት በዓል ለመላዉ የክርስትና እምነት ተከታይ ወገኖቼ እንኳን አደረሳችሁ በማለት ስገልጽ የተሰማኝን ልባዊ ደስታ ከተለየ አክብሮት እና ፍቅር መልዕክት ጋር ነው፡፡
የመስቀል በዓል ከሀይማኖታዊ አስተምህሮቱ እና ከመንፈሳዊ እውነትነቱም ባሻገር የሚያስተምረ እውነት የቱንም ያህል ዘመን፣ በምንም ያህል ውሸትና ሤራ ብትሸፈንም በዘላቂነት ግን ልትቀበር እንደማትችል አይነተኛ ማሳያ ነው፡፡
ዛሬ ከምንም ነገር በላይ ለእውነት የምንቆምበት ጊዜ ላይ እንገኛለን፡፡ በዙሪያችን ብዙ የተሳሳቱ መረጃዎች፣ ስም ማጥፋቶች፣ የሐሰት ወሬዎች፣ አሳሳች አሉባልታዎች እና በስሜት የሚነዱ ማስመሰሎች እንዲሁም ከፋፋይ አስተሳሰቦች ተበራክተውብናል፡፡
እኛ በዓላማ ከጸናን፣ ካልተከፋፈልን ለሐሰተኞች ጆሮና ልቦናችንን ከነፈግን እውነት ብትቀበር እንኳን እንደ ታላቁ መስቀል ሁሉ ቢዘገይም ነጻ እናወጣታለን። የመስቀል በዓል የእንጨቶች ድመራ ነው፡፡ እያንዳንዱ እንጨት ተደምሮ ችቦ ይሠራል፡፡ እያንዳንዱ እንጨት ባንድ ሆኖ ታላቁን ደመራ ይፈጥራል፣ የራሱንም ድርሻ ይወጣል፡፡
ሀገራችን የደመራ ምሳሌ፣ ሁላችንም አንድ ላይ ተደምረን የምንቆምላትና የምንቆምባት፣ ለአንድ ሀገራዊ ዓላማ የምንሰለፍባት ናት። ኢትዮጵያውያን የሚያገጥሙ ችግሮችን እንደ ደመራው ሁሉ አንድ ሆነን ተደምረን በጽናት በማለፍ ከፊታችን የሚጠብቀንን የተስፋ ቀን በጉጉት ልንጠባበቅ ይገባናል ማለታቸውን ከክልሉ መንግስት ኮምዩኒኬሽን የተገኘ መረጃ ያመለክታል።
በድጋሚ መልካም የመስቀል በዓል እንዲሆንልን ከልብ እመኛለሁ፡፡

More Stories
የአፍላ ወጣቶችና ወጣቶችን የስነ ተዋልዶ ጤና ችግሮች ለመቅረፍ የተጀመሩ ጥረቶችን ለማጎልበት የጤና አደረጃጀቶችን ሚና ማሳደግ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ አስታወቀ
ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የመግባት ዕድል ያገኙ ተማሪዎች የበለጠ ውጤታማ ለመሆን ትምህርታቸው ላይ ብቻ ሊያተኩሩ እንደሚገባ መልዕክት ተላለፈ
የሀዲያ ዞን ፋይናንስ መምሪያ ለ2018 በጀት ዓመት ከ10 ቢልዮን ብር በላይ በጀት ለተለያዩ የልማት ስራዎች እንዲውል በተገቢው እንደሚሠራ ገለፀ