የወባ በሽታ ስርጭትን ለመግታት የቁጥጥር ሥራዎችን ማጠናከር እንደሚያስፈልግ ተገለፀ

የወባ በሽታ ስርጭትን ለመግታት የቁጥጥር ሥራዎችን ማጠናከር እንደሚያስፈልግ ተገለፀ

ሀዋሳ፡ መስከረም 15/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የወባ በሽታ ስርጭትን ለመግታት የቁጥጥር ሥራዎችን ማጠናከር እንደሚያስፈልግ ተመላክቷል፡፡

በደቡብ ኦሞ ዞን የዳሰነች ወረዳ ጤና ፅህፈት ቤት የበሽታ መከላከልና መቆጣጠር ሥራ ሂደት ባለሙያ አቶ ሰለሞን ኃይሉ፤ ማህበረሰቡ ራሱን ከወባ በሽታ እንዲከላከል ሙያዊ ድጋፍና ክትትል እንዲሁም የግንዛቤ ትምህርት እየሰጡ መሆናቸው አስረድተዋል፡፡

የዳሰነች ወረዳ ጤና ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ እርቅይሁን ገመዳ እንዳስረዱት፤ በወረዳው የወባ በሽታ ስጋት ያለባቸውን ቀበሌያት በመለየት በልዩ ትከረት እየተሠራ ይገኛል፡፡

ወባን በመከላከልና በመቆጣጠር ረገድ ወረዳው አምና አበረታች ውጤት ማስመዝገቡን ያወሱት የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ አቶ ፍቅሬማሪያም አይመላ የልማት ኮሪደሮችና ወባማ አከባቢዎችን በመለየት ከባለድርሻ አካላት ጋር ይሠራል ብለዋል፡፡

የወባ በሽታን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚረዱ ዘዴዎችን በአግባቡ በመተግበር ጤናቸውን እየጠበቁ መሆናቸውን በደቡብ ኦሞ ዞን የዳሰነች ወረዳ ነዋሪዎች ገልፀዋል፡፡

በዳሰነች ወረዳ ከኦሞራቴ ከተማ ነዋሪዎች መካከል አቶ መለሰ መንገሻ እና ወ/ሮ መዓዛነሽ አድማሱ በጋራ እንደገለፁት፤ የወባ መከላከያ መንገዶችን ተግባራዊ በማድረግ በሽታውን ለመከላል የበኩላቸውን ሚና እየተወጡ ነው፡፡

ዘጋቢ፡ ተመስገን አሰፋ – ከጂንካ ጣቢያችን