300 ለሚሆኑ ወላጅ አጥ ተማሪዎች ኢትዮ- ቴሌኮም ሳውላ ድስትሪክት ከ270 ሺህ ብር በላይ የሚገመት  የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ አደረገ

 የኢትዮ ቴሌኮም ሳውላ ድስትሪክት ስራ አስኪያጅ አቶ ቢልልኝ ሙላቱ ዘንድሮ  ኢትዮ ቴሌኮም በሀገር ደረጃ ”በጎነት ለነገ ተስፋዎች”  በሚል መሪ ቃል ከ430 በላይ ትምህርት ቤቶች ለ70 ሺህ ተማሪዎች ከ72 ነጥብ 9 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ  ለእያንዳንዱ ተማሪ አንዳንድ ደርዘን ደብተር ድጋፍ ማድረጉን ገልፀዋል።

 ድጋፉ መማር ለማይችሉ ወላጅ አጥ ህፃናት እና መማር እየፈለጉ የመማሪያ ቁሳቁስ ላጡ ህፃናት የተደረገ  መሆኑን አንስተው ተማሪዎች ድጋፍ የተደረገውን ደብተር ለታለመለት ዓላማ ብቻ እንዲያውሉ  አሳስበዋል።

በሌላ በኩል በ2016 ዓ.ም በሳውላ ከተማ ውስጥ ከኔትወርክ ተደራሽነትና ከለውጥ ስራ ጋር በተያያዘ እየተነሱ ያሉ ችግሮችን በመለየት ለመፍታት መታቀዱን ተናግረው ህብረተሰቡ በተቋሙ መሰረተ ልማት ላይ ጉዳት የሚያደርሱ አካላትን በጋራ መከላከል እንደሚገባ አሳስበዋል።

 የሳውላ ከተማ አስተዳደር የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብራሃም ብርሃኑ  ኢትዮ ቴሌኮም ህፃናት ወላጅ በማጣትና በአቅም ማነስ የተነሳ በትምህርት ገበታቸው ተረጋግተው እንዳይማሩ የሚያደርገውን በማሰብ 270ሺህ የሚያወጣ ደብተር ድጋፍ በማድረጉ አመስግነዋል።

የሳውላ ከተማ ትምህርት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ጉቼ ሲሳይ ኢትዮ ቴሌኮም ሳውላ ቅርንጫፍ ከዚህ በፊትም ድጋፍ ማድረጉን በማስታወስ ዘንድሮ በኢኮኖሚ ችግር መማር የማይችሉ ተማሪዎችን ከትምህርት ቤት ርዕሰ መምህራን ጋር ከየቀጠናው በመለየት 300 ተማሪዎችን ለኢትዮ ቴሌኮም አቅርበን ድጋፍ በጠየቅነው መሰረት ለሰጡን ምላሽ ምስጋና አቅርበዋል።

ድጋፍ ካገኙ ተማሪዎች መካከል አዳነ ውዴ ፣ሊሊ ጴጥሮስ እና ነፃነት አክልሉ በጋራ የደብተር ዋጋ በመወደዱ ምክንያት መቸገራቸውን በማንሳት ኢትዮ ቴሌኮም ላደረገው ድጋፍ አመስግነዋል።

 ዘጋቢ : ኢያሱ አዲሱ – ከሳውላ ጣቢያችን