ከመኸር እርሻ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ በስልጤ ዞን የአልቾ ውሪሮ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለፁ

 

በወረዳው በተያዘው መኸር ከ 8 ሺ 450  ሄክታር በላይ ማሳ በተለያዩ የሰብል አይነቶች እየለማ መሆኑንም የወረዳው ግብርና ፅ /ቤት አስታውቋል።

መላውን ህዝብ አምርቶ መጋቢ የሆነውን አርሶ አደር ኑሮ ለማሻሻልና የግብርናውን ምርታማነት እድገት የተሻለ ለማጎልበት እንደሀገር ለዘርፋ የተሻሻሉ አሰራሮችና ቴክኖሎጂ ሽግግር ተግባራት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ይገኛል ።

በስልጤ ዞን ደጋማ የአየር ንብረት በተቸረው አልቾ ውሪሮ ወረዳ ገብስን ጨምሮ   የጥራጥሬ ሰብሎችና ድንች በስፋት ይለማል ። 

  አርሶአደሮች ወቅታዊ አማራጮችን ተጠቅመውና የቀረበውን አብቃቅተው በኩታ ገጠም ያለሙት ማሳቸው አሁን ላይ በጥሩ የአበቃቀል ቁመና መገኘት ከዘርፉ ጥሩ ውጤት የማግኘት ተስፋ እንዲሰንቁም ነግረውናል ።

ለምርታማነት ስኬቱም የግብርና ባለሙያዎችን ምክረሃሳብ በመተግበር የዕለት ተዕለት የማሳ ክትትልና ቁጥጥር ስራ አጠናክረው መቀጠላቸውንም አርሶአደሮች  አብራርተዋል ።

በወረዳው በበልግ ልማት ያጋጠመውን የምርት መቀነስ ችግር በሚያካክስ መልኩ ለተያዘው መኸር እርሻ ውጤታማነት ልዩ ትኩረት በመስጠት በአጠቃላይ ከ 8 ሺ 450 ሄክታር በላይ ማሳ በተለያዩ የሰብል አይነቶች መሸፈን መቻሉን የወረዳው ግብርና ፅ /ቤት ኃላፊ አቶ ሱልጣን በርጋ ተናግረዋል ።

ከመደበኛው መኸር እርሻ የታሰበውን የምርታማነት ግብ በተገቢው ለማሳካት   ያስችል ዘንድ እስከ ድህረ ምርት አሰባሰብ  ድረስ ባለው ሂደት የምርት ብክነትን በሚያስቀሩ የተሻሻሉ የቴክኖሎጂ ውጤቶች እገዛ  ለመሰብሰብ ከወዲሁ እየተሰራ መሆኑንም አቶ ሱልጣን አመላክተዋል ።

ዘጋቢ:-አብዱልሃሚድ አወል ከሆሳዕና ጣቢያችን